በአፋር ክልል ዱለሳ ወረዳ በተከሰተ ” የመሬት መንቀጥቀጥ ” ምክንያት ከተፈጠረ የመሬት ስንጥቅ ውስጥ ፍል ውሃ መፍለቅ መጀመሩን የአካባቢው ነዋሪዎች እና የወረዳው አስተዳደር ተናግረዋል።
ከትናንት ሌሊት ጀምሮ መፍለቅ የጀመረው ፍል ውሃ መጠኑ እየጨመረ መሆኑን የአካባቢው ነዋሪዎች ገልጸዋል።
አፋር ክልል ካለፉት ሁለት ሳምንታት ወዲህ ተደጋጋሚ የመሬት መንቀጥቀጥ እያስተናገደ ነው።
በክልሉ ጋቢ ራሱ ዞን በሚገኘው ዱለሳ ወረዳ ሳንጋቶ ቀበሌ ፍል ውሃ መፍለቅ የጀመረው ትናንት ሰኞ መስከረም 27/2016 ዓ.ም. ምሽት ” የመሬት መንቀጥቀጥ ” ከተከሰተ በኋላ እንደሆነ የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሊ ደስታ እና ሁለት የቀበሌው ነዋሪዎች ተናግረዋል።
ነዋሪዎች ምን አሉ ?
– ትናንት ምሽት ሦስት ሰዓት ገደማ መከሰት የጀመረው የመሬት መንቀጥቀጥ ቢያንስ ሶስት ጊዜ ያህል ተደጋግሟል።
– የመሬት መንቀጥቀጥ መከሰቱን የሚናገሩት ካቆመ በኋላ ሌሊት 10 ሰዓት ገደማ ላይ ድምፅ ሰማን። ጠዋት ላይ ድምፅ ወደተሰማበት ቦታ ስናመራ ከመሬት ስንጥቅ ውስጥ ፍል ውሃ እየፈለቀ ተመልክተናል።
– ውሃው የወጣው የአካባቢው ማህበረሰብ በሚኖርበት ሰፈር ውስጥ ነው። ድምፅ ነበረው። ማታ ፈርተን ነው ያደርነው። በጠዋት ሄደን ሁሉንም ነገር ለማየት ችለናል።
– ውሃው በሚወጣበት የመሬት ስንጥቅ ስር ድምፅ ይሰማል። ወደላይ የሚፈናጠረው ፍል ውሃ መጠን እና የሚፈልቅበት ስንጥቅ መጠን እየጨመረ ነው።
ፍል ውሃው በወጣበት ሳንጋቶ ቀበሌ ውስጥ ፍል ውሃ ባለመኖሩ አዲሱ ክስተት ነዋሪዎች ድንጋጤ እና ስጋት ላይ ጥሏል።
የወረዳው አስተዳዳሪ አቶ አሊ ደስታ ምን አሉ ?
° ከትናንት በስቲያ ከተከሰተው የመሬት መንቀጥቀጥ አንጻር የትናንቱ ትንሽ ያነሰ ነው።
° ከዚህ በኃላ ነው ፍል ውሃ መፍለቅ የጀመረው።
° ሰዎች በቅርበት እዚያ አካባቢ ይኖራሉ። የእኛ አካባቢ ማህበረሰብ አርብቶ አደር ከመሆኑ አኳያ ከብቶቻቸውን ፍየሎቻቸውን የሚጠብቁበት ቦታ ነው።
° የወረዳው አስተዳደር ክስተቱን ለማጣራት ባለሙያዎችን ወደ ቀበሌው ልኳል።
° የሚፈጠረው ነገር ስለማይታወቅ ነዋሪዎች’ ከዚያ አካባቢ ለቅቀው ወደ ሌላ ቦታ እንዲሄዱ የማድረግ ስራ እየሰራን ነው። እንደዚህ አይነት ነገር ታይቶም ስለማይታወቅ ከፍተኛ ስጋት ነው ያለው።
የአፋር ክልል ጋቢ ራሱ ዞን በተደጋጋሚ እያጋጠመ ባለው የመሬት መንቀጥቀጥ ምክንያት ነዋሪዎች ከሰፈሩበት አካባቢ እንዲነሱ እየተደረገ ነው።
አንዱ አካባቢው ይኸው የዱለሳ ወረዳ ነው።
አጎራባቹ አዋሽ ፈንታሌ ወረዳ ከሁለት ሳምንት በፊት በአካባቢው በሚገኘው ከሰም ግድብ እና ፈንታሌ ተራራ አካባቢ የሚኖሩ ከ700 በላይ ሰዎችን ገላጣ ሜዳ ወደሆኑ አካባቢዎች አዘዋውሯል።
መረጃው የቢቢሲ አማርኛው አገልግሎት ሲሆን ፎቶና ቪድዮ የአብዶ ሀሰን፣ ሱልጣን ከሚል ነው።
Video ቴሌግራም ላይ ይመልከቱ https://t.me/+f_kxmaPjD-9jYTdk

