ሌላኛው ችግራችን ደግሞ የአዙሪት ሰለባ መሆናችን ነው። የኋላ ታሪካችንን ለጥልና ለንትርክ እንጂ ዞሮ ለማየት፣ ለመማርና ለመሻሻል አልተጠቀምንበትም፣ አካሄዳችንም አዲስ የመፍትሄ ሀሳብ የሚጎድለውና አዝጋሚ በመሆኑ በየጊዜው ለችግሮች ስንዳረግ ቆይተናል። ጦርነትና የፖለቲካ አዙሪትም ለዘመናት የተጣባን ፈተናችን ሆኖ ቆይቷል። በአጠቃላይ ሀገራችን ምሳሌ ከሚሆን የስልጣኔ ባለቤትነት እና ተወዳዳሪነት በእጅጉ ወደኋላ ቀርታለች፣ ይህ የመደመር መንግሥት የቁጭት ማጠንጠኛ ነው።
እንደመንደርደሪያ
የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ አራተኛውን የመደመር መጽሃፍ (የመደመር መንግሥት) በሚል ርዕስ ለንባብ አብቅተዋል።
ይህ መጽሃፍ ለዕውቀት ወይም ለግንዛቤ ብቻ ተነቦ የሚቆም ሳይሆን፤ የሀገራችንን ቀጣይ የማደግ ወይም ያለማደግ እጣ ፈንታ ለመወሰን የሚያስችሉ የፖሊሲ ማዕቀፎችን እና አቅጣጫዎችንም ለመቅረጽ የሚያገለግል የፖሊሲ ሰነድ ነው።
በመሆኑም በመጽሃፉ እያንዳንዱ ክፍል የተጠቀሱ ጉዳዮች በስፋት ሊዳሰሱ፣ ሊመረመሩና ሊተነተኑ ይገባል።
ይህ ጽሁፍ የመጽሃፍ ዳሰሳ ለማለት የሚያስችል አይደለም። ምክንያቱም መጽሃፉ በውስጡ ከያዛቸው ዘርፈብዙ ጉዳዮች አንጻር በቂ ጊዜ ወስዶ በጥልቀት ማንበብን እንዲሁም ከእያንዳንዱ ጉዳይ አንጻር ሌሎች ተዛማጅ ጽሁፎችን ማገላበጥና መመርመርን የሚጠይቅ ነው።
ነገር ግን በመጽሃፉ ውስጥ ከተገለጸው የሐሳብ ባህር ውስጥ ጥቂቱን በመጨለፍ ለመዳሰስ ይሞክራል።
በመሆኑም ለዚህ ዳሰሳ የተመረጠው አካሄድ በመጽሃፉ ላይ የሰፈሩ ዋና ዋና ጉዳዮችን መምዘዝና የራስን መረዳት ማስቀመጥ ነው። በዚህ መሰረት ይህ አጭር ዳሰሳ ስምንት አእማዶችን መዞ በማውጣት በአጭር በአጭሩ ለማብራራት ይሞክራል።
የመደመር መንግሥት መጽሃፍ በሦስት ክፍሎች፣ በ13 ምዕራፎች እና በ78 ርዕሰ ጉዳዮች የተዋቀረ ነው። መጽሃፉ ሁለገብ የፖለቲካ፣ የማህበራዊ፣ የኢኮኖሚና የማህበረሰባዊ ክንውኖችን ሁኔታ ከመሰረቱ ዳስሷል።
መነሻውም የኋላ ታሪካችን ነው። የት ነበርን? የሚለውን ከነትርክቱ ጭምር ተዳስሷል። በዚህም የቀደመው ዘመን ጥንካሬዎቻችን ምን ነበሩ? ድክመቶቻችንስ? የሚሉ ሀሳቦችን በስፋት አንስቷል።
ከዚያስ በኋላ የነበረን ጉዞ ምን ይመስል ነበር? የሚለውንም በማስረጃዎችና በመረጃዎች አስደግፎ አቅርቦልናል።
ለምን ወደኋላ ተመለስን? አሁንስ ያሉብን ፈተናዎች ምንድናቸው? በሚል ከቁጭት በመነሳት ከዚህ ለመውጣት የምንችልባቸውን አማራጭ መንገዶችም አመላክቷል። መጽሀፉ የተከተለው አካሄድም የአመክንዮ አካሄዶችን ነው።
በዚህ መሰረት በዚህ ጽሁፍ የተመረጡት አእማዶች ከኋላ መቅረት፣ መሻገሪያ መንገድ፣ የተሻገረ ገጠር፣ ኢንዱስትሪ፣ የዘመነ ከተማ፣ ቱሪዝም፣ የፖለቲካ ስክነት፣ ሀሳብ አልባ ፖለቲካና የሐሳብ ገበያ የሚሉ ጽንሰሃሳቦች ናቸው።
1. ከኋላ መቅረት
የመደመር መንግሥት መነሻ ቁጭት ነው። ለምን ወደኋላ ቀረን ከሚል ቁጭት ይጀምራል። የኢትዮጵያውያንን ሕይወት መለወጥ ያለፉ መንግስታት ሁሉ መፈክር ሆኖ ቆይቷል።
ሙከራዎችም ተደርገዋል። ነገር ግን ከድህነትና ከኋላ ቀርነት ፈቅ አላደረጉንም፣ ይህ ለምን ሆነ? የሚለው መመርመርና መፈተሽ አለበት። የመደመር መንግሥትም ይህንን ነው ያደረገው? ለምን ወደኋላ ቀረን?
የመደመር መንግሥት ለዚህ ሁለት ምክንያቶችን ያስቀምጣል። አንደኛው የሄድንባቸው መንገዶች ውስንነት ያለባቸው መሆናቸው ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ጉዞአችን የኤሊ መሆኑ ነው።
ከዚህም በመነሳት እነዚህን ወቅቶች የባከኑ ጊዜያት ይላቸዋል። በዚህ በቀደመው ዘመን አንዱ ጉዳይ ከኋላ መቅረት ወይም በጊዜ መቀደም ነው።
ዓለም አራት የኢንዱስትሪ አብዮቶችን አስተናግዶ አምስተኛውን ለመቀበል በዝግጅት ላይ ነው። በነዚህ ሂደቶች ውስጥ ያለው ሽግግር ከጊዜ ወደጊዜ እየፈጠነ መጥቷል።
በቀጣይም ከዚህ በላይ እየፈጠነ እንደሚሄድ ይጠበቃል። ምክንቱም የመጣንበት መንገድ ይህንን የሚያመላክት ነውና።
በግብርና፣ በጤና፣ በምርትና ፈጠራ፣ በመገናኛ ቴክኖሎጂ፣ በጦር ኃይል፣ ወዘተ ዓለም ኢተገማችና በፍጥነት ተለዋዋጭ መሆኑን የመደመር መንግሥት በስፋት ተንትኗል።
በሌላ በኩል ደግሞ ዓለም በእጅጉ የተሳሰረበት ወቅት ነው። በዚህ ዘመን በአንዱ ጫፍ የሆነው ነገር በሌላኛው የዓለም ጫፍ ቶሎ መድረስ ብቻ ሳይሆን ተጽዕኖም ያሳድራል። የአንድ አካባቢ ቀውስ ለሌላው የዓለም ጫፍም ተጽዕኖው እየከበደ መጥቷል።
እኛስ?
ዓለም ከደረሰበት ደረጃ በብዙ ርቀት ላይ ነን። የምሰጠውም ምላሽ አዝጋሚ ነው። እርሻችን ዛሬም ከእንስሳት ትከሻና ከሞፈር ቀንበር አልተላቀቀም፣ ከዝናብ ጥገኝነት አልወጣንም፣ እነዚህ የመደመር መንግሥት የተቆጨባቸው መነሻዎች ናቸው።
በሌላ በኩል ከኢትዮጵያ እኩል የለውጥን መንገድ የተከተሉ ሀገራት ጥለውን መሄዳቸውን ያብራራል። አብነቶችንም ይጠቅሳል።
ዓለም የመጀመርያዎቹን ሦስት የኢዱስትሪ አብዮቶች ስታካሄድ ኢትዮጵያ በፊውዳል ስርዓት ስር ነበረች፣ የፊውዳል ስርዓት ደግሞ ቆሞ ቀር ነው።
በመሆኑም ከዓለም እኩል ለመጓዝ ሳይቻል ቆየ፣ በኋላ ደርግ ሲመጣ ደግሞ ከሶቭየት ህብረት የተኮረጀ ኢንዱስትሪ አብዮትን ነው የተከተለው፣ ይህ አካሄድ ምን ጠንካራና ደካማ ጎኖች ይኖሩታል? ከኛ ነባራዉ ሁኔታ አንጻር ምን ጥንካሬና ድክመት ይኖራል? የህዝባችንስ ሁኔታ እና ስነልቦና ምን ደረጃ ላይ ነው? የሚሉና የመሳሰሉ ጉዳዮችን ከግንዛቤ አላስገባም።
እናም የሚፈለገው ውጤት ሳይመጣ ቀረ። በኋላ ኢህአዴግ ሲመጣ ወደመጨረሻዎቹ አካባቢ ከጀማመራቸው ጥቂት ስራዎች ውጭ ብዙም ውጤታማ አልነበረም። በዚህም የኢንዱስትሪ አብዮታችን አብዮት ብቻ ሆኖ ቀረ።
የስብራታችን ዋነኛ መንስኤዎች ምንድናቸው የሚለውንም መጽሃፉ በዝርዝር ይዳስሳል። ከዚህ አንጻር አንዱ ስብራታችን የሰለጠነ የሰው ኃይል አለመኖር ነው።
በየዘመኑ የኢንዱስትሪውን አብዮት ለማንቀሳቀስ የሚያስችል የሰለጠነ የሰው ኃይል ለማፍራት የሄድንበት ርቀት እዝጋሚና አነስተኛ ነበር።
ሌላኛው ችግራችን ደግሞ የአዙሪት ሰለባ መሆናችን ነው። የኋላ ታሪካችንን ለጥልና ለንትርክ እንጂ ዞሮ ለማየት፣ ለመማርና ለመሻሻል አልተጠቀምንበትም፣ አካሄዳችንም አዲስ የመፍትሄ ሀሳብ የሚጎድለውና አዝጋሚ በመሆኑ በየጊዜው ለችግሮች ስንዳረግ ቆይተናል። ጦርነትና የፖለቲካ አዙሪትም ለዘመናት የተጣባን ፈተናችን ሆኖ ቆይቷል።
በአጠቃላይ ሀገራችን ምሳሌ ከሚሆን የስልጣኔ ባለቤትነት እና ተወዳዳሪነት በእጅጉ ወደኋላ ቀርታለች፣ ይህ የመደመር መንግሥት የቁጭት ማጠንጠኛ ነው።
መጽሃፉ የቀደመውን የውድቀት መንገድ የዓባይን ልጅ ውሀ ጠማው በሚል ርዕስም ገልጾታል። በዚህ ረገድ ችግሮቻችንን በዝርዝር አስቀምጧል። ከነዚህም ውስጥ ትክክለኛውን ጥያቄ አለመጠየቅ አንዱ መንስኤ እንደሆነ ያሳያል።
ለዚህም አንዳንዶቹ የውጭ ሞዴሎችን እንዳለ በማምጣት ለመተግበር መሞከራቸው፣ ኢህአዴግ ደግሞ ብሔርን ከአስተዳደሩ ባለመለየት ጽንፍ ብሄርተኝነትን መውለዱን አትቷል።
በዚህም ሰፊ አቅም እያለን አቅማችን መባከኑ፣ የመሰረተ ልማት እጥረት፣ ሥርዓታዊና መዋቅራዊ ፈተናዎች እንዲሁም ተከታታይ ጦርነቶች እንዳንሻገር ምክንያት መሆናቸውን ዘርዝሯል።
2. የመሻገሪያ መንገድ
የመደመር መንግሥት ችግሮችን በመዘርዘር ብቻ አያቆምም፣ ይልቁንም ችግሮቻችንን እንደ ተሞክሮ በመውሰድ ልንማርባቸው የሚገቡ እንደሆኑ አጽንኦት ሰጥቶ ያነሳል። ከዚህም ባሻገር የሌሎች ሀገራት ተሞክሮ ምን ይመስላል የሚለውንም በስፋት ይዳስሳል።
“የበለጸጉ ሀገራት አሁን ላሉበት ደረጃ የመድረሳቸው አንዱ ሚስጢር በየትውልዱና በየዘመኑ የተከማቸ ወረት መኖሩ ነው” የመደመር መንግሥት፤ ገጽ 79
እኛ ቀደም ሲል በርካታ እድሎች ከእጃችን አምልጠውናል። ለዚህ ደግሞ በየዘመኑ አፍርሶ የመገንባት አባዜ የተጠናወተን መሆኑ አንዱ በሽታ መሆኑን የመደመር መንግሥት ያምናል።
በሌላ በኩል ቀደም ሲል የነበሩ አብዮቶች እውን የሆኑት በጊዜ ሂደት ነው። ምዕራባውያን ለማደግ ከ200 እስከ 300 ዓመት ሲፈጅባቸው፣ በቅርቡ ደግሞ የሩቅ ምስራቅ ሀገራት ከ30 እስከ 40 አመት ነው የፈጀባቸው።
ይህም የጊዜ አስፈላጊነት እየጨመረ መምጣቱን ያመላክታል። ስለዚህ ከዚህ በኋላ ለመለወጥ መሮጥ ብቻ ሳይሆን መብረር እንደሚገባ መጽሃፉ አጽንኦት ሰጥቷል።
በዚህ ሂደት ውስጥ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ሥርዓት አካሄዳችን ለእድገት ልዩነት መሰረት መሆኑን የመደመር መንግሥት ያምናል። ሆኖም በሀገራችን የመንግሥት መዋቅሩ ደካማ መሆኑን ይገልጻል።
“በሀገራችን መንግሥት ቀርፋፋና ቅልጥፍና የሌለው ነው። በሌላ በኩል ደግሞ የግሉም ክፍለ ኢኮኖሚ ተወዳዳሪነት ይጎድለዋል፤ ነጻ ተቋማትና ጠንካራ ቢሮክራሲ አልዳበሩም፣ ሥራዎች አዝጋሚ በሆነ መንገድና በተለምዶ ይከናወናሉ፤ ከውጤት ጋር የመተሳሰር ችግርም አለባቸው” የመደመር መንግሥት፤ ገጽ 110
ከዚህ አንጻር የመደመር መንግሥት ምን አስቧል? የሚለው ጥያቄ ይነሳል። ለዚህም በመጽሃፉ በግልጽ ተመላክቷል።
የመደመር መንግሥት ዋና ግብ የማይበገር ኢኮኖሚ፣ በታቀደ አግባብ ደረጃ በደረጃ መፍጠር ነው። የወደፊቱን የሚያሰላ፣ ተለዋዋጭ ሁኔታዎችን ተቋቁሞ እንደመልካም አጋጣሚ ወስዶ እድገቱን ማስቀጠል የሚችል እንደሆነ አብራርቷል።
ለዚህም ምናባዊ ከፍታ ያለው፣ የማድረግ አቅም የገነባ፣ ተለማጭነትና ተላማጅነትን የሚተገብር፣ በቅንጅት የሚሰራ፣ ክፍተትን የሚሞላ አካሄድ የሚከተል፣ ገበያን የሚፈጥር ንቁ ኢንቨስተርን የሚያሳትፍ፣ መዋቅራዊ ሽግግርን መምራት የሚችል፣ አደጋን ተቋቁሞ አይበገሬ ኢኮኖሚ ለመገንባት ቆርጦ የተነሳ እና መሰረታዊ ችግሮችን በድፍረት የመፍታት ወኔ ያለው እንደሆነ ይገልጻል።
3. የተሻገረ ገጠር
ኢትየጵያን ግብርናን የጀመረች ሀገር ብትሆንም ለዘመናት ከበሬ ትከሻ እና የተፈጥሮ ዝናብን ጠብቆ በአመት አንድ ጊዜ ከማረስ አልተላቀቀችም። በመሆኑም ግብርናን ከዚህ ፈተና ማውጣት የመደመር መንግሥት ሌላኛው ግብ ነው።
በዚህ ረገድ ግብርናችን በሜካናይዜሽን የሚታገዝ፣ የግብዓት አቅርቦቱ የተሟላና የዘመኑን ቴክኖሎጂ የታጠቀ መሆን እንዳለበት ያምናል።
ከዚህም በተጨማሪ እንደ አምራች፣ ቱሪዝም እና ሌሎች አገልግሎት ዘርፉ ላይ ላሉ ዘርፎች ያለው ትስስር መዳበር እንዳለበት በግልጽ አስቀምጧል።
በዚህም ምርትን በጥራት፣ በብዛትና በአይነት ማምረት እንዲሁም የገበያ ትስስርን በመፍጠር ዘርፉ እንዲያድግ ትልቅ ትኩረት ይሰጣል።
ከዚህ ጋር የተያያዙት የማይበገር አረንጓዴ አሻራ ኢኮኖሚን የመገንባት ትልም፣ የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር፣ የእንስሳት ሀብት ልማት እና መሰል ጉዳዮች ትኩረት ይሰጣቸዋል።
4. ኢንዱስትሪ
ኢንዱስትሪ አንዱ የመደመር መንግሥት ምሰሶ ነው። በዚህ ረገድ መጽኃፉ ዘርፉ ያለፈባቸውን መንገዶች በዝርዝር ዳስሷል። በተለይ በቀደመው ዘመን በዚህ ረገድ የነበርንበትን ከፍታ ማጣታችንን መጽሃፉ በቁጭት ያነሳል።
ከሳንቲም መገበያያነት አሞሌን ወደመጠቀም፣ በዝሆን ከሚጎተት ሰረገላ ወደ አጋሰስ መጓጓዣ፣ ከድንጋይ ውቅር ቤተመንግሥት ወደሳር ጎጆ ወዘተ የወረድንባቸው ስብራቶች የሚያስቆጩ እንደሆኑ ያስቀምጣል።
ከኢንዱስትሪ አንጻር የነበረው አመለካከትም የተዛባ መሆኑን ያትታል። ለአብነትም ጥሬ እቃ፣ ያልተነካ ታዳሽ ሀይል፣ ሰፊ የሰው ጉልበት ወዘተ ስላለን እንደመጽናኛ የምናይበት ሁኔታ እንደነበር ይገልጻል። ሆኖም ይህ አሁን ባለው የቴክኖሎጂ ዘመን ጊዜ ያለፈበት ነው። ዛሬ በሮቦት ብዙ ስራ መስራት ይቻላል፤ ከትንሽ ጥሬ እቃ ብዙ ማምረትም ይቻላል፤ ወዘተ።
እነዚህን ችግሮች የሚዳስሰው የመደመር መንግሥት የኢንዱስትሪ አካሄዳችን በዋናነት ዐውዳችንን ያገናዘበ፣ ዛሬ ካለን ወረት ተነስቶ የነገን ግዙፍና በዓለም አቀፍ መድረክ ተወዳዳሪ ኢንዱስትሪን በፈጠራና በፍጥነት መገንባትና ዘላቂነቱን ማስጠበቅን የተለመ ነው።
በመሆኑም ግቡ በገቢ ንግድ ወደሀገራችን የሚጎርፉ ሸቀጦችን በሀገር ውስጥ ምርት የመተካት አካሄድን የሚከተል ነው።
5. የዘመነ ከተማ
ከተማና ከተሜነት ከመደመር መንግሥት መገለጫ ባህርያት አንዱ ነው። ኢትዮጵያ ከከተማ ምስረታ አንጻር የቀደመ ታሪክ ቢኖራትም በየዘመኑ መንግስታት ሲቀያየሩ ከተሞቹም አብረው እየተቀየሩ አፍርሶ የመገንባት እጣ ፈንታ እነሱንም ሲጎበኝ ኖሯል።
በዚህም ከተሞቻችን ሰፋፊ ገጠሮች ሆነዋል። የሚጠበቅባቸውንም መሰረተ ልማት ያሟሉ አይደሉም። ከዚህም በተጨማሪ ዛሬም በርካታ ዜጎቻችን በገጠር ይኖራሉ።
የመደመር መንግሥት ይህ ታሪክ ማብቃት እንዳለበት ያምናል። በዚህም በከተሞች እንደ ውሃ፣ መብራት፣ የፍሳሽ መሰረተ ልማት፣ ጤናና ትምህርትን የመሳሰሉ መሰረታዊ ፍላጎቶችን በጥራት ማቅረብ እንደሚገባ ያምናል፤ ለዚህም ይሰራል። በዚህም የኮሪደር ልማት ስራ የመደመር መንግሥት ከተሞችን ለመቀየር ከጀመራቸው ተግባርት አንዱ እንደሆነ ይጠቅሳል።
6. ቱሪዝም
የመደመር መንግሥት በአጭር ጊዜ መሰረታዊ ለውጥ ካስመዘገበባቸው ዘርፎች አንዱ ቱሪዝም ነው። ሆኖም ይህ ዘርፍ ኢትዮጵያ ካላት ሰፊ ሀብት አንጻር የሚጠበቀውን ያህል አለማደረጉ ይታመናል።
ከዳሎል እስከዳሽን ተራራ ያለ መልከአ ምድር ፣ በርካታ ታሪኮች፣ ብዝሀ ባህል፣ ተፈጥሮና የመሳሰሉ ሀብቶች ቢኖረንም በሚገባው ልክ ሳንጠቀምበት ኖረናል።
ይህንን ለመቀየር በአራት ኪሎ ቤተመንግሥት የተጀመረው የገበታ ለሸገር የልማት ስራ በገበታ ለትውልድም በርካታ ለውጦችን አምጥቷል።
“ተስፋን መትከል፣ አቧራን ማራራገፍ፣ ውበትን መግለጽ” በሚል መሪ ሀሳብ የተጀመረው ይህ ፕሮጀክት የበርካታ ከተሞችን አቧራ አራግፎ ውበታቸውን ገልጧል፤ ተስፋም አላብሷቸዋል።
አድዋ ሙዚየምን፣ ብሄራዊ ቤተመንግሥትን፣ ሳይንስ ሙዚየምን እና ሌሎች በርካታ የቱሪዝም መስህቦችን እውን ማድረግም አስችሏል።
ይህ ዘርፍ በርካታ እድሎችን ከፊቱ የያዘ ነው። ለዚህም የዓለም የቱሪዝም ኢንዱስትሪ እያደገ መምጣቱ፣ ቀጣይም የማደግ ተስፋ ያለው መሆኑ፣ ዓለምን ለማገናኘት የሚያስችሉ የምድርና የአየር ትራንሰፖርት መሰረተ ልማቶች እየተስፋፉ መምጣታቸው እንዲሁም አዲስ አበባ የዲፕሎማት ከተማ እየሆነች መምጣቷ ማሳያዎች ናቸው። እነዚህን በአግባቡ መጠቀም ከተቻለ ከዚህ ዘርፍ ብልጽግና ይወለዳል።
7. የፖለቲካ ስክነት
በሀገራችን የፖለቲካ አለመረጋጋት ለዘመናት ያልተላቀቀን ሾተላይ ነው። አንዱ መንግሥት ሄዶ ሌለው ሲተካ አፍርሶ ከዜሮ መጀመር አንዱ ባህላችን ከሆነ ሰንብቷል።
ከዚህም አልፎ እኔ ስልጣን ካላገኘሁ አልያም የጥቅም ተጋሪ ካልሆንኩ ምናገባኝ የሚለው አመለካከት የሀገራችን የፖለቲካ አካሄድ ሆኖ ኖሯል።
ሀገርንም ወደኋላ ሲጎትት ቆይቷል። ከራስ የተሻገረ የፖለቲካ ዓላማ ጠፍቶ እኔ ከሌለሁ ሁሉም ይጥፋ የሚል አመለካከት ሀገርን ሲጎዳ ኖሯል። የመደመር መንግሥትም ይህንን በሚገባ አስቀምጧል።
“ክፉ ልማድ ከሰይጣን ይብሳል ይባላል። ሥርዓታዊ በሆነ መንገድ ሥርዓትን የመለወጥ በጎ ልማዳችን አናሳ ነው። በዚህ የተነሳ አብዮት ከደማችን ጋር ተዋህዷል።
ይህ ደግሞ ቶሎ ወደጽንፍ ይወስደናል። የ2010ሩ ለውጥም ፈተናው ይህ ነው። “ሕገመንግስቱ ይቀደድ”፣ እና “ፈጽሞ እንዳይነካ” በሚሉ ቡድኖች መካከል ያለው ዋልታ ረገጥ እንቅስቃሴ፣ ለፖለቲካ አለመረጋጋትና ለፖለቲካ አለመግባባት ዋናው መንስኤ ሆኖ ይታያል”
የመደመር መንግሥት፤ ገጽ 286
ይህንን ከመሰረቱ መቀየር የመደመር መንግሥት ዋነኛ የትኩረት አጀንዳ ነው።
8. ሀሳብ አልባ ፖለቲካ
በኢትዮጵያ ለፖለቲካ አለመረጋጋት አንዱ መንስኤ በሀሳብ የበላይነት የሚያምን እና የሚያሳምን ፖለቲከኛ ማጣታችን ነው።
መሰረታዊ የሀገራችንን ችግሮች ለይቶ ህዝብን ከችግሩ ለማውጣት የሚያስችል የሰላና የተደራጀ ሀሳብ ማመንጨትና በሀሳብ ላይ ተመስርቶ የወደፊቱን ሀገራዊ ራዕይ ለማሳካት የሚያስችል ስርዓት መፍጠር የሚችል ፖለቲከኛ እንዳለመታደል ሀኖ ሀገራችን ለማፍራት ስትቸገር ኖራለች። ይህ የወለደው ፈተናም ሀገርን ከድጡ ወደማጡ እንድትጓዝ ሲያደርግ ኖሯል።
ሀሳብ አልባ ፖለቲካ ሀብትንና ሥልጣንን ኢመደበኛና ህገወጥ በሆነ መንገድ ለመቀራመት የሚደረግ ሙከራ ነው። በዚህም የጥቅም ትስስርን መፍጠር ዋነኛ አካሄዱ ነው።
የዚህ አይነት ፖለቲካ መዳረሻው የሰዎችን ፍላጎት መሰረት ያደረገ ቡድናዊ መሻትን እያቀጣጠለ ሥርዓትና ህግን በመጣስ የራስን ጥቅም ማስጠበቅ ነው። ፍላጎቱም የኢኮኖሚ፣ የሀይል እና ያልተገባ ክብር ነው።
ሀሳብ አልባ ፖለቲካ ተቋማዊ አቅም እንዳይፈጠር፣ ያለውም እንዳያድግና እንዲዳከም ያደርጋል። የተቋማት ድቀትንም ያስከትላል። የተከፋፈለ ፖለቲካዊ ማህበረሰብንም ይፈጥራል።
መንግሥትነትም ከምርጫ ይልቅ ወደሽያጭ፣ ከሀሳብ ይልቅ ትግል ላይ የተንጠለጠለ፣ መፈንቅለ መንግሥት አማራጩ የሚያደርግ እንዲሁም በፖለቲካ ነጋዴዎች የተጠለፈ ነው።
የመደመር መንግሥት ይህንን ከመሰረቱ ለመለወጥ የሀሳብ ገበያ እንዲዳብር ትልቅ ትኩረት ሰጥቶ ይሰራል።
የሀሳብ ገበያ ፖለቲካዊ እምነትና ይሁንታን ከማንነት ሚዛን ሳይሆን ከሐሳብና ከውጤት ሚዛን የሚመነጭበት ፖለቲካ ነው።
የለውጡ መንግሥት የሐሳብ ገበያን ለማጎልበት ሐሳብ አልባ ፖለቲከኞች የሚደበቁባቸውን ምሽጎች በህግ እንዲመሩ በማድረግ የማስተካከል፣ ሚዛንን የመጠበቅ፣ ሐገራዊ ምክክርን ቅድሚያ የመስጠት እንዲሁም የህዝብ መድረኮችን በማስፋት የሀሳብ የበላይነት የሚነግስበትን መንገድ ይከተላል።
ማጠቃለያ
የመደመር መንግሥት የኢትዮጵን ነባራዊ ሁኔታ ከአሕጉርና ዓለምአቀፍ ነባራዊ ሁኔታ አንጻር እያስቃኘ የሚተነትን በመሆኑ ሰፊ ባህር ነው። እናም በዚህ ዳሰሳ የተጠቀሱት ሀሳቦች ከባህሩ የተጨለፉ ቅንጣቶች ናቸው።
እኛ የስልጣኔ ጀማሪዎች ሆነን ወደፊት መጓዝ ካልሆነም በዚያው መቀጠል ያቃተንና ይባስ ብሎ ወደኋላ የተንሸራተትነው ለምንድነው? ለምን የአዙሪት ሰለባ ሆንን? መዘግየት፣ መንሸራተትና መጥፋት እጣ ፈንታችን ለምን ሆነ? የሚለው የመጽሃፉ ጭብጥ አካል ነው።
በዚህም ወደኋላ ከመለሱን ችግሮቻችን ውስጥ አንዱ መንግስታት ሲለዋወጡ አፍርሶ እንደ አዲስ የመጀመር አባዜ የተጠናወታቸው መሆኑን በዝርዝር ዳስሷል።
በሌላም በኩል በየዘመኑ የመጡ ስርዓቶች የሀገራቸውን ነባራዊ ሁኔታ በአግባቡ ተገንዝበው እና ከሌላው ትምህርት ወስደው የነበረውን ከማስቀጠልና እያደጉ ከመሄድ ይልቅ ሁሉም በየፊናው መጓዝን ነው የመረጠው።
የፖለቲካ አካሄዳችንም የውጭውን እንደወረደ ኮርጆ የመተግበር አባዜ የተጠናወተው በመሆኑ ውጤት እንዳናመጣ አድርጎናል።
የባከነ እምቅ አቅም፣ የመሰረተ ልማት እጥረት፣ ሥርዓታዊና መዋቅራዊ ፈተናዎች እንዲሁም ጦርነትና ግጭት ከኋላ ለመቅረታችን ዋነኛ መንስኤዎች መሆናቸውን የመደመር መንግሥት በጽኑ ያምናል።
በሌላ በኩል ተስፋዎቻችንንም በልኩ ያነሳል። ኢትዮጵያ ወደፊት ለመጓዝ የሚያስችሉ በርካታ ተስፋዎችም አሏት። እነዚህን እድሎች እንደ መልካም እድሎች እንዴት እንጠቀምባቸው የሚለው መሰረታዊ ጥያቄ ነው።
የመደመር መንግሥት ቁጭታችንን ለመማሪያነት፣ መልካም እድሎቻችንን ለመስፈንጠሪያነት በመጠቀም ከብልጽግና ጎራ ለመቀላቀል የሁላችንም ጥረት እንደሚያስፈልግ በአጽንኦት ተንትኗል። የእያንዳንዳችንንም ድርሻ አስቀምጧል።
እርስ በርስ ከመጠላለፍ እና ከሐሳብ አልባ ፖለቲካ ወጥተን በሀሳብ ገበያ ውስጥ መግባትና ሀገርን ማሻገር ከእያንዳንዱ ዜጋ የሚጠበቅ ተግባር ነው።
ከተቸነከረ አስተሳሰብ መላቀቅና ወደፊት አሻጋሮ ማየት ይገባል። ለዚህም ራዕይ መጋራት ይገባል። በዚህ ሂደት ውስጥ ደግሞ የፖለቲካ ስክነት ያስፈልጋል።
የመደመር መንግሥት አሁን የጀመራቸው የብልጽግና ተስፋዎችን እውን ለማድረግና የባከነውን ጊዜ ለማካካስ መፍጠር፣ መፍጠንና መዝለል እንደሚገባ በአጽንኦት ተንትኗል።
ከጋዜጣ ፕላስ የተወሰደ

