ኢትዮጵያ የባህር በር ለማግኘት እየሄደችበት ያለው አግባብ በወጉ የታሰበበት ይመስላል። የኤርትራን ዕንቅልፍና የመሪዋን ክፋት አሽቀንጥሮ በመጣል ወደ ሶማሊላንድ ያመራው የኢትዮጵያ መንግስት ከዜናው ጀርባ ሊኖር እንደሚችል፣ ወዳጁን አረብ ኤምሬትስን ተጠቅሞ ሊሆን እንደሚችል በርካቶች ከግምት በላይ ይገልጻሉ። ገና ወደ ስልጣን እንደመጡ በማግስቱ ትህነግና ሻዕቢያ ያፈረሱትን ባህር ኃይል የገነቡት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ፣ ስለ ባህር በር ሲናገሩ የተቹ ነበሩ። አስቀድመው መዘጋጀታቸው እየታወቀ ‘ማዘናጊያ’ በሚል በርካቶች አፋቸውን ሲጉመጠመጡም ነበር። እነዚህ ወገኖች እስራኤል ወደ ሶማሊላንድ ስትመታ ምን ይሉ ይሆን? የደህንነት ጉዳይ ኔትናሁ ሲያነሱት ትክክል፣ አብይ ሲያነሱት ውግዝ …
ኢራን ሊባኖስ ላይ የሚካሄደውን ወረራና የሄዝቦላህ መሪ ነስረላህ ግድያን ለመበቀል በእስራኤል ላይ የሚሳይል ናዳ ማዝነቧንና በኢራን የሚደገፈው የየመኑ ሀውቲ ታጣቂ በመርከቦች ላይ የሚፈጽመው ጥቃት እያየለ መሄዱን ተከትሎ እስራኤል በሶማሌላንድ የጦር ሰፈር ለመገንባት መወሰኗን ይፋ ያደረገው ጄሩሳሌን ፖስት ነው።
እስራኤል ከየመን ሃውቲ ታጣቂዎች ለሚከፈትባት ጥቃትና ማናቸውም ስጋት ማብረጃ እንዲሆን በርበራ ወደብ ላይ የጦር ሰፈር መገንባት እንዳስፈለጋት በርካታ የመገናኛ ብዙሃን ጽፈዋል። በኢትዮጵያ ጥብቅ ወዳጅ የተባበሩት ኤምሬትስ አግባቢነት የእስራኤል ወደ ባብኢልማንደብ ወይም ህንድ ውቅያኖስ ማንቁርት ለማቅናት መወሰኗ ሲሰማ ጎን ለጎን ደግሞ በህንድ ውቅያኒስ ላይ ኢራንና ሩስያ “አይኤምኢኤክስ 2024” የተሰኘው የጦር ልምምድ ማድረጋቸው ታውቋል። ዓላማው በቀጣናው የጋራ ደህንነትን ለማረጋገጥና የወታደራዊ ደህንነትን የሚያጸና ወዳጅነትን ለማሳየት መሆኑን ሮይተርስ በዘገባው አመልክቷል።
“እስራኤል በሶማሌላንድ ላይ የጦር ሰፈር ለመገንባት ፍላጎት ይፋ አደረገች” በሚል የተሰማው ዜና ለኢትዮጵያ ትርጉም ያለው መሆኑ ደግሞ ዜናው በቀይ ባህር ዙሪያ ህብረት መፍተራቸውን ለሚናገሩ የሰሞኑ ፍቅረኞች መርዶ እንደሆነም ተሰምቷል።
የጦር ሰፈር ግንባታው የሃውቲ አማፂያን በቀይ ባህር የሚፈፀሙትን ጥቃት ለመከላከል፣ የባብ ኢል-ማንዳብ ስትሬት ደኅንነትን ለመጠበቅ እና በቀጣናው የሚፈፀሙ ወንጆሎቸን ለመከላከል ያለመ ነው። ይህ ዜና ኢትዮጵያ ከሶማሊላንድ ጋር የጀመረችውን የባህር በርና የጦር ሰፈር የመገንባት ስምምነት ጋር በቀጥታ ያገናኙ እንዳሉት ዜናው ለኢትዮጵያ በርካታ ዕድሎችን ይዞ የሚመጣ ነው።
ኢስት ሞኒተር እንዳለው ይህ የእስራኤል ውሳኔ ለሶማሌላንድ እውቅና በመሥጠት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ተፈጥራለች። የእስራኤል ወደ ባብኢልማንደብ ማምራት ግብጽ፣ ኤርትራና መሃል ከተማዋንና እንኳን መቆጣጠር ያልቻለው የሃሰን ሼኽ መንግስት ለፈጸሙት “ቡቱቶ ጥምረት” የሞት መርዶ ሆኗል።
መረጃዎች እንደሚያሳዩት በምሥራቅ አፍሪካ ስትራቴጂክ ከሚባሉ አካባቢዎች አንዷ የሆነችው ሶማሌላንድ፣ አንድ ሦስተኛው የዓለማችን የባሕር ንግድ ዝውውር ይከናወንባታል። ሶማሌላንድ ከኤደን ባሕረ ሰላጤ በ740 ኪሎ ሜትር ርቀት የምትገኝ ሲሆን የባብ ኢል-ማንዳብ መስመር እና ቀይ ባሕርን ደኅንነት፣ ከሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር፣ የባሕር ላይ ውንብድናና ሌሎች የሽብር ጥቃቶች ለመካለከል ቁልፍ መስመር እንደሆነች ባለሙያዎች በተደጋጋሚ መናገራቸው አይዘነጋም።
በዚህ ቁልፍ መስመር ላይ ኢትዮጵያ የባህር ኃይሏን አስፍራለች። ውሉ ይፋ እስከሚሆን የሚተብቅ ሆኖ እንጂ ጉዳዩ አልቋል። ዛሬ ላይ የተሰማው ዜና ይፋ ከመሆኑ በፊት እስራኤል የኢትዮጵያን በርበራ ወደብ ላይ መስፈርና የጦር ሰፈር መገንባት እንደምትደግፍ በርካታ መረጃዎች ሲወጡ ነበር። ዝግጅት ክፍላችን ኢትዮጵያዊ ዲፕሎማትን በመጥቀስ እስራኤል የኢትዮጵያን እንቅስቃሴ እንደምትደግፍ፣ አሜሪካንም ተመሳሳይ አቋም እንዳላት፣ ከአውሮፓ ቁልፍ የሚባሉት አገሮችም ተመሳሳይ አቋም እንዳላቸው በነገሩን መሰረት አትመን ነበር።
ሚድል ኢስት ሞኒቶር ሶማሊላንድ በኤደን ባህረ ሰላጤ 740 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የባህር ጠረፍ ያላት፣ የባብ አል ማንዳብ ባህርንና ቀይ ባህርን ከባህር ወንበዴዎች፣ ሽብርተኝነት እና ህገወጥ የሰዎች ዝውውር ለመጠበቅ ቁልፍ ሚና ለመጫወት የሚያስችል ምቹ ሁኔታ የያዘች አገር መሆኗን ጠቅሶ፣ የአረብ ኤምሬትስንና የእስራኤልን ወዳጅነት አመልክቷል።
የየመን ሁቲዎች ባደረሱት ጥቃት፣ ዓለም አቀፍ የንግድ እንቅስቃሴን በማስተጓጎላቸው፣የተለያዩ ዓለም አቀፍ የመርከብ ኩባንያዎች በባብ አል-ማንዳብ በቀጥታ አቋርጠው የነጋዴ መርከቦችን ለማከራየት እያመነቱ ነው።
ነጋዴዎች የፍጆታ ዕቃዎችን ወደ ቸርቻሪዎች ለማድረስ አማራጭ የማጓጓዣ መንገዶችን ለማግኘት ደፋ ቀና ቢሉም ሌሎች አማራጮች በአፍሪካ የሚደረጉ ጉዞዎች በግምት ከተለመደው በተጨማሪ በአስር ቀን የሚያራዝም ሆኖ አግኝተዋታል። ይህን ጉዳይ ኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ከስጋት አንጻር ታነሳለች። በአንድ ጅቡቲ የተቸከለችውና የባህር በር አልባ የሆነቸው ኢትዮጵያ በርበራ ላይ የራሷን የባህር በር ለማግኘት የወሰንችበት ውሳኔና ጊዜ በበርካቶች ዘንዳ በበጎ ታይቷል።
የኢትዮጵያን በጎ በሚያስቡ ወገኖች በበጎና በአድናቆት የታየው ይህ እርምጃ፣ በአንዳንድ ተቃዋሚዎችና ከኤርትራ መንግስት ጋር አብረው እንደሚሰሩ ከሚታወቁ “ኢትዮጵያዊያን” ዘንዳ ተቃውሞ ሲያስተናግድ መቆየቱ አይዘነጋም። አሜሪካ ጣልቃ እንድትገባ የጠየቁም አሉ።
በ2023 መገባደጃ ላይ የዩኤስ የመከላከያ ሚኒስትር ሎይድ ኦስቲን እ.ኤ.አ. በ2023 ኦፕሬሽን ብልጽግና መከላከል የሚል ህብረት መቋቋሙን አስታውቀው እንደነበር ፣ በዚህም የአዲስ የብዝሃዓለም አቀፍ ደህንነት ተነሳሽነት ህብረት ውስጥ እንደ እንግሊዝ፣ ፈረንሳይ፣ አሜሪካ እና ጣሊያን ያሉ ቁልፍ ሀገራትን የሚሳተፉበት እንደሆነ መዘገቡ አይዘነጋም። ይህ ህብረት የየመን አማጺያኖች የፈጠሩት ስጋት የወለደው ነው።
እንደ ዘገባው ከሆነ እስራኤል ደህንነቷን በሩቅ ለመጠበቅና፣ከዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ሊመነጩ ከሚችሉ ሌሎች ኢኮኖሚያዊ እድሎች ጋር አጣምራ በየመን የሁቲዎችን ህልውና ለማምከን ዕቅድ ይዛለች።
የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች ከእስራኤልና ከሶማሌላንድ ጋር ግንኙነት አላት፣ ከ2017 ጀምሮ በሶማሊላንድ የጦር ሰፈሯን አቋቁማለች። የተባበሩት አረብ ኢሚሬቶች ለሶማሊላንድ ሪፐብሊክ እውቅና ከሰጡ የቀጣናው ሀገራት መካከል አንዷ ስትሆን በመካከለኛው ምስራቅ ሰፊ ኢንቨስትመንት እንዳላት ሞኒተር ጽፏል።
የተባበሩት አረብ ኢሚሬቶች እስራኤል በሶማሊላንድ ወታደራዊ ሰፈር ማቋቋም እንድትችል በእስራኤል ስም የማግባባት ስራ እየሰራች መሆኑን ሚድል ኢስት ሞኒተር ዲፕሎማሲቲክ ምንጮችን ጠቅሶ ዘግቧል።
ኢትዮጵያና የተባበሩት አረብ ኢምሬትስ አሁን ላይ ካላቸው ጥብቅ ትስስር አንሳር፣ በሶማሊላንድ የበርበራ ወደብን ከማስተዳደራቸውና ለአገሪቱ የገቢ ምንጭ እንደመሆናቸው፣ ከበርበራ ወደ ኢትዮጵያ የሚዘልቀውን 234 ኪሜ ርዝመት ያለው ይህ መንገድ በ400 ሚሊዮን ዶላር እንዲገነባ ያደረገች አገር እንደመሆኗ ዜናው ለኢትዮጵያ ታላቅ ብስራት እንደሆነ ጉዳዩን የሚከታተሉ ይናገራሉ።
ኢትዮጵያ ሃያ ኪሎሜትር እርዛማኔ ያለውንና በአካባቢው ጥልቅ እንደሆነ ከሚነገርለት የባብኤልማንደብ ቁልፍ የውሃ አካል ለመያዝ ስምምነት ማድረጓ ይፋ ሲሆን ኤርትራ በይፋ ማውገዟ ይታወሳል። በአባይ ግድብ ላይ የምትችለውን ሁሉ ሞክራ ያልተሳካላት ግብጽ ይህንኑ እንደምክንያት ተጠቅማ ሶማሌ ውስጥ በመግባት ሁከት ለመፍጠር ላይ ታች በምትልበት በአሁኑ ወቅት እስራኤል ወደ ሶማሊላንድ ማቅናቷ ለኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ጡንቻ ይጨምራል። በተጻራራሪው ግብጽን አደብ የሚያስገዛ እንደሆነ አስተያየት እየተሰጠ ነው። ግብጽ ከአሜሪካ በየዓመቱ በቢሊዮን የሚቆተር የብርና የመሳሪያ ድጋፍ የሚደረግላት አገር እንደሆነች ይታወሳል። ኤርትራና ሶማሊያ በጉዳይ ላይ እዚህ ግባ የሚባል ዋጋ እንደሌላቸው የሚገልጹ ወገኖች ዜናውን “ድል” ብለውታል።
የአሜሪካና ኤምሬትስ “ዋንኛ የመከላከያ አጋርነት” ስምምነት ኢትዮጵያን ወደ ቀይ ባህር የሚመልስ አረንጓዴ መብራት እንደሆነ ጠቅሰን መዘገባችን አይዘነጋም።
አርብ ኤምሬትስ የአሜሪካ ሁለተኛዋ ”ዋነኛ የመከላከያ አጋር” መሆኗን አሜሪካ አስታወቀች። ሁለቱ አገራት ወታደራዊ ስምምነት ያደረጉት በዋናነት “በመካከለኛው ምስራቅ፣ ምስራቅ አፍሪካ እና ህንድ ውቅያኖስ ክልል ወታደራዊ ትብብርን ይበልጥ የሚያጎለብት ነው” ሲል ዋይትሃውስ አጋርነቱን አጉልቶ በመግለጫው አመልክቷል። ዜናው ለኢትዮጵያ መልካም ብስራት እንደሆነ ጉዳዩን የሚከታተሉ ገልጸዋል። ሙሉውን ዘገባ እዚህ ላይ ተጭነው ያንብቡ።’


