በፋሽስት ጣልያን ወረራ ወቅት በጣሊያን ወታደሮች የተወሰደውን የኢትዮጵያዊው አርበኛ ራስ ደስታ ዳምጠውን የወርቅ ሜዳሊያ ለማስመለስ ቤተሰቦቹ ጥረት እያደረጉ መሆኑ ተገለጸ፡፡
ይህ የሆነው በተያዘው ወር መጀመሪያ አካባቢ ቅርሱ ለጨረታ መቅረቡን ተከትሎ ነው፡፡ ቅርሱ መሸጥ ሳይችል መቅረቱን መረጃዎች አመላክተዋል፡፡ ከወርቅ የተሰራውና ጠንካራው ባለኮኮብ ሜዳሊያ በአጼ ኃይለሥላሴ አማች እና የኢትዮጵያ አርበኞች የጦር አዛዥ የነበሩት ራስ ደስታ ዳምጠው እጅ የነበረ ሲሆን፤ አርበኛው በ1937 በመያዛቸውና በመገደላቸው ኢትዮጵያ በፋሽስት ላይ የነበራትን ተቃውሞ ማክተሚያ እንዳረገውም ተመላክቷል፡፡
ከ60 ሺህ ፓውንድ እስከ 90ሺህ ፓውንድ የተገመተው የኮኮብ ቅርጽ ያለው ይህ ቅርስ ለጨረታ ሽያጭ በይፋ እስከወጣበት ጊዜ ድረስ የት እንዳለ አይታወቅም ነበር፡፡ የጀግናው ዓርበኛ የልጅ ልጅ የሆነችው ላሊ ካሳ ስለጉዳዩ ስትሰማ የተሰማትን ስትገልጽ “የመጀመሪያ ስሜቴ ንዴት ነበር፤ ከገደሉት ሰው ይህንን ወስደናል ብለው በይፋ መናገራቸውም በጣም አስቀያሚ ከመሆኑ የተነሳ እንደ ቤተሰብ ሀዘን ተሰምቶን ነበር፡፡ የሆነውን ነገር ማረጋገጥ ነበረብን” ብላለች፡፡
የቅርስ ማስመለስ ባለሙያ እና የአርት ሪከቨሪ ኢንተርናሽናል መስራች እንዲሁም የቤተሰቡ ጠበቃ ከሆኑት ክሪስ ማሪኔሎ፣ ጋር ቅርሱ እንዲመለስ በነጻ እየሠሩ መሆናቸውም ገልጻለች፡፡ ማሪኔሎ ቅርሱን ለማስመለስ ጥያቄ ቢያቀርብም ሜዳሊያው በ61 ሺህ 595 ፓውንድ ለሽያጭ ቀርቦ ነበር ብላለች፡፡ በታህሳስ 1 ቀን በተካሄደው ጨረታ ንብረቱ ለአሸናፊነት የሚጠየቀውን ዝቅተኛ ዋጋ ማሟላት ባለመቻሉ አሁን ከራስ ደስታ ዳምጠው ቤተሰብ ህጋዊ ተወካይ ጋር በቀጥታ ውይይት እየተደረገበት ይገኛል፡፡
በኒውዮርክ የጆን ጄይ የወንጀል ፍትህ ኮሌጅ ተባባሪ የታሪክ ፕሮፌሰር የሆኑት ጀምስ ደ ሎሬንዚ እንዳሉት ሜዳሊያውን ልዩ የሚያደርገው ከኢትዮጵያ የወጣበትና የተገኘበት መንገድ ከጦር ወንጀል ጋር በቀጥታ የተያያዘ ሊሆን እንደሚችል ነው። በ1936 ዓ.ም አጼ ኃይለ ሥላሴ ወደ እንግሊዝ ለስደት ሲሄዱ የጣሊያንን ወረራ ለመዋጋት የወሰነው ዓርበኛ ራስ ደስታ ዳምጠው፤ የካቲት 24 ቀን 1937 በጉራጌ ዞን በሚገኝ አንድ ተራራ አካባቢ በተፈጠረ ግጭት ተይዘው በፋሽስት ጣሊያን መኮንኖች በሚመራ ተዋጊ ቡድን ተገድለዋል፡፡
እ.ኤ.አ. በ1948 የኢትዮጵያ መንግስት 10 የጣሊያን ዜጎችን በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጦር ወንጀለኞች ኮሚሽን ፊት ክስ አቅርቦ በጦርነት እስረኛ ሆነው ሳለ የተገደሉትን የራስ ደስታ ዳምጠውን ግድያ የሚገልፅ ሰነድ አቅርቦ ነበር። ይህ ማስረጃ 10 ጣሊያኖችን በጦር ወንጀለኞች የተጠረጠሩ ናቸው ብሎ እንዲወሰንባቸው አድርጓል። “በዚህም ሜዳሊያውን ያገኘው በዚህ የጦር ወንጀል ውስጥ ቀጥተኛ ተሳትፎ ባለው የፋሺስት አገዛዝ ወኪል ሲሆን ይህም በጅምላ ግድያ፣ ጾታዊ ጥቃት፣ ማሰቃየት እና የዘፈቀደ እስራትን ባሳተፈ ሰፊ የፀረ-ፋሽስት ትግል ውጊያ ወቅት ነበር” ሲል ዴ ሎሬንዚ ተናግሯል፡፡
የራስ ደስታ ዳምጠው የልጅ ልጅ ላሊ ካሳ፣ ሜዳሊያው በሚመለስበት ጊዜ በግል እንደማይካሄድ ጠቅሳ፤ “ሜዳሊያውን መመለስ ከቻልን በአዲስ አበባ በሚገኘው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም በቋሚነት እንዲታይ እንፈልጋለን ” ብላለች፡፡
የኢትዮጵያ ባለኮከብ የወርቅ ቅርስ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ወደ ምስራቅ አፍሪካ ሲመለስ የመጀመሪያው ውድ ቅርስ ባይሆንም፤ ምናልባት ጣሊያን አቢሲኒያ ተብሎ ይጠራ የነበረውን ቦታ በወረራ በያዘችበት ጊዜ የዘረፈቻቸው እቃዎች የት እንዳሉ ለማወቅ አዲስ ፍላጎት እንደሚፈጥር ተገልጿል፡፡ እ.ኤ.አ. በ1947 የተፈረመው የፓሪስ የሰላም ስምምነት አንቀጽ 37 ጣሊያን በ18 ወራት ውስጥ “ከጥቅምት 3 ቀን 1935 ጀምሮ ከኢትዮጵያ የተወሰዱ የኢትዮጵያውያን የጥበብ ሥራዎች፣ ሃይማኖታዊ ቅርሶች መዛግብት እና ታሪካዊ ዋጋ ያላቸው ዕቃዎችን ወደ ኢትዮጵያ መመለስ አለባት” ይላል። ነገር ግን የጣሊያን መንግስት የራስ ደስታ ዳምጠውን ጨምሮ ሳይመለሰሉ የቀሩ በርካታ ቅርሶች አሉ፡፡
| ዘ ጋርዲያን እንደዘገበው vis gazetteplus

