ብታምኑም ባታምኑም!
አዲስ ዓመትን እንዲያከብሩ እስረኞችን ፈቶ የለቀቀው ፖሊስ በቁጥጥር ስር ዋለ፡፡
ድርጊቱ ፈገግታን ቢጭርም በስካር መንፈስ ውስጥ ሆኖ የአዲስ አመት ዋዜማን እንዲያከብሩ 13 ታሳሪዎችን ከፖሊስ ጣቢያ የለቀቀው የፖሊስ አባል በቁጥጥር ስር ውሎ የሀገሪቱ ፖሊስ የተለቀቁትን እስረኞች እያፈላለገ ነው ተብሏል፡፡
የዛምቢያ ፖሊስ አባል የሆነው መርማሪ ኢንስፔክተር ቲተስ ፊሪ የተባለው ፖሊስ በቁጥጥር ስር የሚገኙ ተጠርጣሪዎቹን በዋና ከተማዋ ሉሳካ ከሚገኘው ሊዮናርድ ቼሎ ፖሊስ ጣቢያ ነው ፈቶ የለቀቃቸው፡፡
ለረጅም ሰአታት በጠጣው መጠጥ በአልኮል ተጽዕኖ ውስጥ የነበረው ኢንስፔክተሩ ድርጊቱን ከፈጸመ በኋላ ከህግ ለማምለጥ ጥረት አድርጓል፡፡
ባልጠበቁት ሁኔታ ከእስር ቤት እንዲወጡ የተፈቀደላቸው ታሳሪዎች በዝርፊያ ፣ ስርቆት እና አካላዊ ጥቃት በማድረስ ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር የሚገኙ ነበሩ፡፡
በአሁኑ ወቅት ሉሳካ የሚገኘው የሊዮናርድ ቼሎ ፖሊስ ጣቢያ ፖሊስ አባላት ያመለጡትን ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር ለማዋል በአደን ላይ ይገኛሉ፡፡
የፖሊስ ቃል አቀባይ ሬ ሀሙንጋ ድርጊቱን የፈጸመው ኢንስፔክተር ቲተስ ፊሪ በአዲስ አመት ዋዜማ ተረኛ የእስረኞች ጠባቂ ከሆነችው የፖሊስ አባል የእስር ቤቶቹን ቁልፍ በሀይል እንደቀማት ተናግረዋል፡፡
በመቀጠልም ኢንስፔክተሩ የወንድ እና ሴት የእስር ቤት ክፍሎችን በመክፈት “ወደ አዲሱ አመት ለመሻገር ነፃ ሆናችኋል” በማለት ከእስር ቤቱ እንዲወጡ እንዳዘዛቸው ቃል አቀባዩ ገልጸዋል፡፡
በስካር መንፈስ ውስጥ ሆኖ ያልተጠበቀውን ድርጊት የፈጸመው መርማሪ ኢንስፔክተር ወዲያው ከአካባቢው ለመሸሽ ቢሞክርም በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውሏል፡፡
ኢንስፔክተሩ ድርጊቱን ለምን እንደፈጸመ እስካሁን ቃሉን እንዳልሰጠ የተገለጸ ሲሆን ፖሊስ በበኩሉ ከእስረኞቹ መለቀቅ ጀርባ የስካር ስህተት ወይስ ድብቅ ዓላማ ያለው የተቀነባባረ ድርጊት የሚለውን ለማጣራት በምርመራ ላይ እገኛለሁ ብሏል፡፡
Via – አልአይን

