እነ ጃዋር ታስረው ኦሮሞ ዝም ብሎ የተቀመጠው ለምንድን ነው? እንዴት አልተነሳም?
ባለፈው እንዳልኳችሁ ቤተልሔም ታፈሰ የአንዳንድ ፖለቲከኞች ጓዳቸውን ለአደበባይ አብቅታባቸዋለች። ከዚህ ውስጥ ለየት ባለ መልኩ የተደነቀችበት አንድ ሰው ቢኖር ልደቱ አያሌውን ነው።
እንዲህ ትላለች፦
ልደቱ ከእስር ከወጣ በኋላ ቢደውልልኝ፥ ነገሩ እንግዳ ሆኖብኝ ግር አለኝ። ብዙ ፖለቲከኞች፦ በፕሮግራሜ እንግዳ ሁኑ እንዳልል ይሆናል፥ እምብዛም ስልክ አይደውሉልኝም። ምናልባት በወቅቱ ከቴሌቪዥን ሥራ ውጪ ስለነበርኩም ይሆናል ልደቱ የደወለልኝ።
ከሁለት ቀናት በኋላ ኢሊሊ ሆቴል ምሳ እንድንበላ ጋበዘኝ። ነገሩ በጣም ከነከነኝ። ለምን ፈለገኝ? ለአንድ ጓደኛዬ ደወልኩ፦
“ልደቱ ምሳ ጋብዞኛል። ከኔ ምን ፈልጎ ነው? ምሳ የሚያገባብዝ ቅርበት የለንም።” አልኩት።
“ግማሽ ቀን ስጪኝ።” አለኝ።
በማግስቱ ጠዋት ደወለ፦
“ልደቱ ብዙ ቦታዎች እየደወለ ቀጠሮ እየያዘ ነው። ቤቲ፥ መረጃ ፈልጎ ነው የሚሆነው።” አለኝ።
ቀኑ ደርሶ ሄድኩ። ቀድሞኝ ደርሷል።
ኢሊሊ ሆቴል፦
ኢሊሊ ሆቴል፥ የኦሮሞ ብሄረተኞች የሚያዘወትሩት ቤት ነው፡፡ ምክንያቱን ባላውቅም፥ ልደቱም ቤተኛ መሆኑን አውቃለሁ፡፡ አስረኛ ፎቅ ወዳለው ምግብ ቤት ወጣሁ። አስተናጋጇ መጣች። የተወጠረ አጭር ቀሚስ አድርጋለች። ዚፑ እንዴት ተዘጋላት ይሆን? ሙሉ ለሙሉ ሰውነቷ ላይ የተጣበቀ ነበር።
ምሳ ስናዝ ቤተሰብ መሆኑን በሚያመለከት መልኩ፦
“ያ የዶሮ ሥጋ…” ሲል፥ አስተናጋጇ ወዲያው አወቀች።
“በሚያቃጥል ፈሳሽ የሚጠብሱት ዶሮ ነው።” አለኝ።
እኔም ምሳዬን አዘዝኩ። በፀጥታ በላንና ሰሃኖች ተነሱልን። ቡና ለመጠጣት ወደ ታች ወረድን።
ቡና መጣልን።
ቀጥታ ጥያቄውን ፍርጥ አደረገው:-
“እነ ጃዋር ታስረው ኦሮሞ ዝም ብሎ የተቀመጠው ለምንድን ነው? እንዴት አልተነሳም?” አለኝ።
ስኒው ከእጄ ሊከነበል ምንም አልቀረው! ደግሞ ይህን ጥያቄ ለመመለስ እኔ ማን ነኝ? ምን አውቅና ነው? የሚል ጥያቄ ጭንቅላቴ ውስጥ ደወለብኝ። እኔ ምን አውቃለሁ? ልል አልኩና፥ አይ አውቃለሁ… አልኩ ለራሴ መልሼ። ምን አውቃለሁ? ብዬ አስቤ ሳልጨርስ፥ አውቅ የለም እንዴ? በሚለው ሀሳብ መተካቱ ራሴን ለአፍታ እንድፈራው አደረገኝ። ስኒውን ቀስ ብዬ አስቀመጥኩት።
“ግራ ገብቶኝ ነው ምንድነው?” አለኝ፡፡
“ግራ የገባህ ኦሮሞ ዝም ማለቱ ነው?”
“አዎ! እነ ጃዋር ታስረው ኦሮሞ እንዴት ቤቱ ገብቶ ዝም አለ?”
“ግምቶች ናቸው ያሉኝ።” አልኩት፦
“ግምት ነው ያለኝ፤ ይህ ግምት ግን ከእውነትና ከእርግጠኝነት ምንም አይተናነስም ብዬ አምናለሁ።” ቡናዬን በመሃል ፉት አልኩና፦
“አንደኛው፥ ኦሮሞ ይሀን መንግሥት እገለብጣለሁ ብሎ አይነሳም። ሊያለቃቅስ ይችላል፣ ሊያኮርፍ ይችላል፣ ዳቦ አላገኘሁም ይህንና ይህን አላደረጋችሁልኝም ሊል ይችላል፤ ጨክኖ ግን ውረዱልኝ! የሚል አመጽ ያስነሳል ብዬ አላምንም።”
“ለምን?” አለኝ።
“ኦሮሞ፥ ይህ መንግሥት የኔ ነው ብሎ ያምናል።” አልኩት። እኔም ራሴ እንደዚያ እንደማምን ሳልነግረው ግን ቀረሁ፡፡
”ሁለተኛውስ?” አለኝ፡፡
“ለሁለተኛው ግምቴ የማሳይህ ማስረጃ የለኝም። ለውጡ እንዲፋፋም ሲገፉና የአደባባይ ሰልፎችን ሲያቀጣጥሉ የነበሩት፣ ከጃዋርም አፍ የማይጠፉትና እሳት ይተፉ የነበሩት፣ በታንከ በለው በስናይፐር ፊት እጃቸውን እያጣመሩ በሰላማዊ ትግል የወደቁት፥ በተለምዶ ቄሮ የሚባሉት የኦሮሞ ወጣቶች፥ የጃዋር ቄሮዎች አይደሉም!” አልኩት፡፡ ክው ብሎ ደነገጠ። በእርግጥ ራሴም ደንግጫለሁ፡፡
“ማለት?”
“ያንን አመጽ ያደራጀው ኦህዴድ ነበር። ያ ወጣት የጃዋር ወጣት አልነበረም። ጃዋርን ሊወደው ሊያደንቀው ይችላል። ጠላት እንዲነካውም አይፈቅድ ይሆናል፤ አደረጃጀቱ ግን የጃዋር ሳይሆን የኦህዴድ ነበር። ቄሮን አደራጅቶ፥ መመሪያ ደግሞም ከለላ ሰጥቶ አደባባይ የሚያወጣው ኦህዴድ ነበር! ራሴም፥ ጃዋር ግቡ ውጡ ሲል ወጣቶቹ የሚታዘዙት ይመስለኝ ነበር። ቆይቼ ሲገባኝ ተሳስቻለሁ! እንደ ተባለው፥ ቄሮ የጃዋር ኃይል ቢሆን ኖሮ ኦሮሚያ እንዲህ በቀን እንቅልፍ አታሸልብም ነበር።” አልኩት።
ጃዋርና ልደቱ፥ “ከመስከረም 30 በኋላ መንግሥት የለም!”
ከሚለው _ ጥምረታቸውና _ ቅስቀሳቸው በኋላ ዳግም የተገናኙ
አይመስልም፡፡ ለጃዋር የሰጠው ከፍተኛ ግምት የተሳሳተ እንደ ነበረ የሚያረጋግጥለትን ምከንያት ሲፈልግ የነበረ ይመስል፥ እኔ በሰነዘርኩት ሀሳብ ላይ ተቃውሞ አላሰማም። ዓይኖቹን አንድ ቦታ ላይ ተከሎ ዝም አለ፡፡
ሁለቱም ምልከታዎቼ ይጣሙት አይጣሙት አላውቅም፤ እኔም ሀሳቤን እንዴት እንዳየው አልጠየቅሁትም። ጠየቀኝ፥ በጣም ተስፋ በሚያስቆርጥ መንገድ ሊሆን ይችላል፤ የገባኝን ነገርኩት፡፡ ሌላ ሰው ይህን በግልጽ ሊነግረው አይችልም፡፡
“ኦሮሚያ ለምን ዝም አለች?” ቢባል፦
“መቼ ዝም አልን! ወለጋ ትጥቅ ትግል አለ አይደለም እንዴ?” ብሎ እንደሚመልስለት አውቃለሁ፡፡ ይህ ለልደቱ ጠፍቶት አይደለም። እሱ መስማት የፈለገው፥ እሳት የነደደበትና የጋመ የወንበር ግልበጣ ለምን እንዳልተደረገ ነው፡፡ እኔ ደግሞ፥ ራሴም የማምንበትን፦
“ሰዎቹ’ኮ ኦሮሞዎች ናቸው፤ ኦሮሞ ሊገለብጣቸው አይፈልግም!” አልኩት።
ቄሮን ጃዋር ያዘዋል ብሎ ሊያምን ይችላል። ሌላ ሰው ይህን ቢጠየቅ፥ መንግሥት ወጣቶቹ እንዳይታገሉ እያሰረ፣ እያጎረ ነው ብሎ ሊመልስለት ይችላል፤ እኔ ግን ጃዋር ቄሮ እንደሌለው አረጋግጬ ነገርኩት።
ብዙ አልቆየንም፤ አመስግኜው ሄድኩ። እርሱም ኢትዮጵያ ብዙ አልቆየም፤ ለህክምና ወጣ። (ገፅ 36-41)
Via Henok leyekun


