በቅርቡ የተቋቋመው የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር በስምምነቱ የቃል ኪዳን ሰነድ መሠረት አካታች ሊሆን እንደሚገባ የኢሮብ ማህበረሰብ ሲቪክ ማህበር ዋና ዳይሬክተር እና ፖለቲከኛ አቶ ስዩም ዮሐንስ አመለከቱ ። አሁን ላይ የተዋቀረው ካቢኔ የአንድ ቡድን አባላትን ብቻ ያቀፈ መሆኑን አስታወቁ፡፡
አቶ ስዩም ዮሐንስ ለአዲስ ዘመን እንደገለጹት፤ በጊዜያዊ መስተዳድሩ እንዲተገበሩ ከተዘረዘሩት የቃል ኪዳን ነጥቦች መካከል በክልሉ አካታች ለቀጣይ ምርጫ መሠረት የሚጥል ፍትሐዊ አስተዳደር እንዲዋቀር፣ የክልሉ ሰብአዊ እና ዲሞክራሲያዊ መብቶች እንዲከበሩ፣ወንጀል የፈፀሙ ግለሰቦች ተጠያቂ እንዲሆኑ እና የኢትዮጵያ ሉአላዊነት እንዲከበር የሚጠይቅ ነው፡፡
በአቶ ጌታቸው ረዳ ሲመራ የነበረው የቀደመው ጊዜያዊ አስተዳደር የተወሰኑ ያልተሟሉ ነገሮች ቢኖሩትም፤ በተለይ ሰላምን ከማፅናት ጋር ተያይዞ ጠንካራ ሥራ መሠራቱን በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶክተር) እና በሕዝቡ የተመሰከረለት እንደነበር አስታውሰዋል።
አሁን የተዋቀረው ካቢኔ ከበፊቱ እጅግ የከፋ እና አካታችነት ያልሆነ እና የሕዝብ ቅቡልነት የሌለው እንደሆነ አመልክተዋል። በአጭር ጊዜ ውስጥ እየታዩ ያሉ ምልክቶች ክልሉን እና ሕዝቡን ወደ ሌላ አስቸጋሪ መንገድ የሚወስዱ መሆናቸውንም ጠቁመዋል፡፡
የክልሉ ፕሬዚዳንት ሌተናል ጀነራል ታደሰ ወረደ፤ ከፌዴራል መንግሥት ጋር የገቡት ባለ ስምንት ነጥብ የቃል ኪዳን ውል በአጭሩ ሲተረጎም፤በክልሉ የዲሞክራሲ ሥርዓት ለማሸጋገር የሚረዳ እና የተገኘውን የሰላም አየር አጠናክሮ ለማስቀጠል የሚረዳ ፍኖተ ካርታ እንደሆነ አስታውቀዋል፡፡
ጊዜያዊ መስተዳድሩ ለአንድ ዓመት እንዲራዘም በአዋጅ መሻሻሉ በትግራይ ክልል የፖለቲካ፣ኢኮኖሚ እና ማህበራዊ ሁኔታዎች ወደ ተሻለ ሁኔታ ለማድረስ እና የሕዝቡ ሰላም እንዲጠበቅ ቢሆንም ጀነራሉ ያዋቀሩት ካቤኔ እና እየሄዱት ያለው አካሄድ የነበረውን ሰላም የሚያሳጣ ነው ብለዋል፡፡
“እኔ የጠበቅኩት ሁሉንም ያማከለ አቃፊ አስተዳደር ተዋቅሮ የነበሩት ክፍተቶች በሂደት እና በአሠራር ይቀረፋሉ ብዬ ነበር፤ አሁን የተዋቀረው ካቢኔ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ የሕወሓት ቡድን ያቀፈ ነው፤በፖለቲካ እና በአስተዳደር ሥራ ላይ የሕዝብ፣ የሲቪክ ማህበራት እና የፖለቲካ ድርጅቶች ቅቡልነት፣ ከሌለ የፖለቲካዊ ውድቀት ማስከተሉ የማይቀር ነው። ፀረ ሕዝብ መንገድ በመሆኑም የጦርነት ወሬ ማስነገሩ አይቀሬ ነው” ብለዋል፡፡
ጀነራል ታደሰ ወረደ ላለፉት ሁለት ዓመታት በነበራቸው ከፍተኛ የሥራ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እየተወጡ አልነበረም ያሉት አቶ ስዩም፤ በዚህም ምክንያት ፕሬዚዳንት ሆነው ሲመረጡ፤ ምርጫው በአብዛኛው ትግራዋይ ዘንድ ቅቡልነት እንዳልነበረው አስታውቀዋል።
ወታደር በመሆናቸው መወሰን ያለባቸው ጉዳይ ላይ ሊወስኑ ይችሉ ይሆናል፤ አዲስ አካታች ካቢኔ ያዋቅራሉ የሚል ተስፋም በሕዝቡ እና በፖለቲከኞች ዘንድ ተጠብቆ ነበር ያሉት አቶ ስዩም፤ እየሆነ ያለው ግን የተጠበቀው ነው ብለዋል፡፡
ሔርሞን ፍቃዱ ENA⁷

