የብሔራዊ ባንክ ገዥ ማሞ ምህረቱ በሚወጥለው ዓመት የዋጋ ንረትን ለማውረድ በጥብቅ እንደሚሰራ አመለከቱ። በተገባደደው በጀት ዓመት የዋጋ ግሽበትን ወደ 14 በመቶ ዝቅ ማድረግ መቻሉንም አስታውቀዋል። አቶ ማሞ ይህን ያሉት የአስራ አንድ ወራት እቅድ አፈጻጸም ሪፖርትን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ባቀረቡበት ወቅት ነው።
እየተመዘገባ ያለው የግሽበት መቀነስ ይበልጥ እንደሚሰራበት ያመለከቱት የባንኩ ገዢ የዋጋ ንረትን ለመቆጣጠር ምርታማናትን ማሳደግ፣ የውጭ ምንዛሬ ግኝትን በማሳደኛ ወደ ኢኮኖሚው ውስጥ በማስገባት የገባያ ማረጋጋት ስራ ከቁጥጥር ጋር ጎን ለጎን እንደሚሰራ ነው ያመለከቱት።
ብሔራዊ ባንክ ላለፉት አስራ አንድ ወራት በተገበረው ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲ አማካይነት የዋጋ ግሽበትን መቀነስ መቻሉን አቶ ማሞ ምህረቱ አመልክተዋል። በዚሁ ጥብቅ አሰራር ባለፉት አስራ አንድ ወራት ለመንግስት ይሰጥ የነበረውን የብድር ምጣኔ ወደ ዜሮ ማውረድ መቻሉን ለምክር ቤቱ አስረድተዋል። ይህ ማለት በግብር አሰባሰቡ ላይ በተደረገ መሻሻል መንግስት ገቢውን በማሳደጉ ገንዘብ ሚኒስቴር ብድር አልጠየቀም። በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ራሱን ችሏል።
ብሔራዊ ባንክ ውጤት ካስመዘገበባቸው ዘርፎች መካከል የውጭ ምንዛሪ አስተዳደር አንዱ መሆኑን ጠቅሰው፣ በዚህም በትይዩ ገበያና በባንኮች የውጭ ምንዛሪ መካከል የነበረውን ልዩነት ማጥበብ እንደተቻለ ጠቅሰዋል፡፡ እንዲሁም በውጭ ምንዛሪ አስተዳደር አጠቃላይ ገቢን ወደ 32 ነጥብ 1 ቢሊየን ዶላር ከፍ ማድረግ መቻሉን አመልክተዋል፡፡
የሀገር ውስጥ የውጭ ምንዛሪ ክምችትን ማሳደግ፣ ለግል ዘርፎች የሚቀርበውን የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት መጨመር፣ ዕዳ የመክፈል አቅምን የማሳደግና መሰል ትሩፋቶች መገኘታቸውንም የባንኩ ገዢ አስታውቀዋል።
የባንኩን የ2017 በጀት ዓመት የአስራ አንድ ወራት የሥራ አፈፃፀም የገመገመው በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የዋጋ ንረትን ለመቆጣጠር እየተገበረ ያለውን ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲ አጠናክሮ እንዲያስቀጥል አስገንዝቧል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ማሞ ምህረቱ የተቋሙን የገንዘብ ፖሊሲ፣ የዋጋ ግሽበትን ለመቀነስ ስለ ተወሰዱ እርምጃዎች፣ የውጭ ምንዛሬ ሪፎርሙ ያስገኘውን ውጤት ጨምሮ የባንኩን የሥራ አፈፃፀም ሙሉ ሪፖርት ለኮሚቴው ቀርቧል።
በማብራሪያቸውም ኢትዮጵያ ዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገት ማስመዝገብ የሚያስችሉ የሪፎርም ተግባራትን ማከናወኗን አምልክተዋል። በተያዘው በጀት ዓመት የኢኮኖሚ ጫናን በመቋቋም በፊሲካልና በገንዘብ ፖሊሲ እንዲሁም በውጭ ምንዛሬ ግኝት ውጤታማ ስራ መከናወኑን ገልጸዋል።
የገንዘብ ፖሊሲ ማሻሻያው የዋጋ ንረትና የኑሮ ውድነትን በማረጋጋት በኩል ጉልህ ሚና እንዳለው አንስተው፣ ባንኩ በዚህ ዓመት ለመጀመሪያ ጊዜ ምንም አይነት ብድር ለመንግስት አለመስጠቱን አመልክተዋል። ዋጋ ንረቱ በዘላቂነት መፍትሔ እስኪያገኝም ባንኩ የሚከተለውን ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲ አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
ከሃምሳ ዓመታት በላይ ጥብቅ ቁጥጥር ሲደረግበት የነበረው የውጭ ምንዛሬ አስተዳደር ስርዓት በገበያ እንዲወሰን በመደረጉ ትልቅ ስኬት ማስመዝገቡን ገልጸዋል። በዚህም በህጋዊ እና በትይዩ ገበያው መካከል የነበረውን ከፍተኛ ልዩነት በማጥበብ ወደ ኢኮኖሚው የሚገባው የውጭ ምንዛሬ እንዲጨምር ማድረጉን ነው ያብራሩት። በአሁኑ ጊዜ የባንክ ዘርፉ በሁሉም መመዘኛዎች ጤናማ የሚባል መሆኑንም ነው አስረድተዋል።
ይሁንና አንዳንድ ባንኮች የጥሬ ገንዘብ አጥረት የሚፈጥሩት በራሳቸው የአሰራር ክፍተት መሆኑንና ባንኩ ይህን ለማስተካከል የእርምት እርምጃ እየወሰደ ስለመሆኑ አብራርተዋል።
የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጆ፣ ባንኩ በተለያዩ ዘርፎች ያከናወናቸው የሪፎርም ሥራዎች የኢኮኖሚ መረጋጋት እንዲፈጠር ጉልህ ሚና መጫወታቸውን ተናግረዋል።
ባንኩ በበጀት ዓመቱ አዋጆችን በማሻሻል በተለያዩ ዘርፎች ያከናወናቸው የሪፎርም ሥራዎች ተጨባጭ ውጤቶች የተመዘገበባቸው መሆኑን ቋሚ ኮሚቴው በጠንካራ ጎን መውሰዱን አንስተዋል።
በተለይም የዋጋ ንረትን ለመቆጣጠር ከተወሰዱ እርምጃዎች መካከል ለመንግስት የሚሰጠውን ብድር ማስቀረት መቻሉ ትልቅ ውጤት አምጥቷል ብለዋል።
በተያዘው በጀት ዓመት የባንኮች ተቀማጭ ገንዘብ እና መጠባበቂያ የውጭ ምንዛሬ ክምችቱ ከፍተኛ ዕድገት ማስመዝገቡ የሪፍርሙ ውጤት ማሳያ እንደሆነ ጠቅሰዋል። ባንኩ የዋጋ ንረትን ለመቆጣጠር ተግባራዊ ያደረገውን ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲ አጠናክሮ እንዲቀጥል አስገንዝበዋል።
የውጭ ባንኮችን ሥራ ማስጀመር የሚያስችል መመሪያ መውጣቱን ተከትሎ የሀገር ውስጥ ባንኮች ተወዳዳሪ የሚሆኑበትን የድጋፍ አማራጮች መፈለግ እንደሚገባም ነው የቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢው ያመለከቱት።

