በኢቲቪ ኦፋን ኦሮሞ ቴሌቪዥን ከሚቀርበው “ገመዳ ሾው” ጋር ቆይታ ያደረገችው አትሌት ገለቴ ቡርቃ “አደባባይ የወጣሁት ሕዝቤ ያለሁበትን አስቸጋሪ ሁኔታ አውቆ እንዲደርስልኝ ነው” ብላለች፡፡
ከ800 እስከ ማራቶን ኢትዮጵያን ወክላ በተለያዩ መድረኮች የተወዳደረችው አትሌት ገለቴ ሳላውቅ ትዳሬ እየፈረሰ ነውም ብላለች፡፡
“በሩጫ ባገኘሁት ገንዘብ ወደ ኢንቨስትመንት ልገባ ስል ችግር አጋጥሞኛል” የምትለው አትሌቷ.፣ ባለቤቷ በ2009 ዓ.ም ከቤት ጠፍቶ ስምንት ወር ከቆየ በኋላ ፍርድ ቤት እንዳቀረባት እና እስካሁን ክርክር ላይ እንዳሉ ተናግራለች፡፡
ዘጠኝ ዓመታት አብራ የቆየችው ባለቤቷ በ2009 ዓ.ም ለውድድር ከሀገር ውጭ ስትሄድ ከሸኛት በኋላ ውድድሯን ጨርሳ ስትመለስ ባዶ ቤት እንዳገኘች ገልጻለች፡፡
ፍለጋውን ጀምራ ለፖሊስ ስታስታውቅ “ደውሎ ለምን ስሜን ታጠፊያለሽ? አርፈሽ የማትቀመጪ ከሆነ እገድልሻለሁ” እንዳላት የተናገረችው ገለቴ በ2010 ዓ.ም በእርሱ በኩል የክስ መጥሪያ እንደደረሳት ጠቅሳለች፡፡
ፍርድ ቤት ስትቀርብም ባለቤቷ ጋብቻቸው እንዲፈርስ እንደጠየቀ እሷ ደግሞ የተጋቡት በእምነት ተቋም እንደሆነ እና እምነት ደግሞ ጋብቻ እንዲፈርስ እንደማይፈቅድ ጠቅሳ አላፈርስም እንዳለች ነገር ግን በጫና ጋብቻው እንደፈረሰ ትናገራለች፡፡
“ከዚያ ቀደም የወሰደውን ውክልና ተጠቅሞ ያለውን ንብረቴን ሸጦ ስለነበረ ጋብቻው ከፈረሰ በኋላ ንብረቴን ለማሳገድ ብንቀሳቀስም ከአንድ ቤት በስተቀር ሁሉም ስማቸው ዞሮ ነበር ያገኘሁት” ብላለች አትሌት ገለቴ፡፡
አንዷ የቀረችው ቤትም በ2008 ዓ.ም ውክልናው የተነሳባት ቤት እንደሆነ የጠቀሰችው አትሌቷ፣ በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ አሥር ቤቶች፣ አራት መኪና እና ሌሎች በርካት ንብረቶችን ተሸጠውባት ባዶ እጇን መቅረቷን ተናግራለች፡፡
“እናቱ እንዲኖሩበት የሰጠሁትን መንግሥት የሰጠኝን ቤት እንኳን ለእናቱ ሸጧል” የምትለው ገለቴ፣ “ከጋብቻ በፊት ያፈራሁት ንብረቴም ሳይመለስ፣ ከጋብቻ በኋላ ያፈራነውንም ሳልካፈል አንዷን የቀረችውን ቤት ለመካፈል ፍርድ ቤት ወስኖብኛል” ስትል ተናግራለች፡፡
እሱ ቀድሞ ሁሉንም አቅዶበት ስለሄደበት ያላትን አቅም ሁሉ ተጠቅማ ፍርድ ቤት ብትከራከርም ውሳኔው ግን ከሷ በተቃራኒ እንደሆነ ተናግራለች፡፡
ከዚህ አልፎም እንደሚያስፋራራት ለፖሊስ ማልከቷን ጠቅሳ፣ ንብረቱም እንዳይገኝ አንድም ገንዘቡን በሱ ስም እንደማያስቀምጥ እንዲሁም ተሸጡ የተባሉ ንብረቶችም ከዋጋቸው እጅግ ባነሰ የተሸጡ መሆናቸው ጉዳዩን ውስብስብ እንዳደረገው ተናግራለች፡፡
ይህን ጉዳይ የማያውቀው የመንግሥት አካል እንደሌለ የጠቀሰችው አትሌት ገለቴ፣ “እስካሁን መፍትሄ ካለማግኘቴም በላይ ወደ ጎዳና ለመውጣት ከዚያም አልፎ ለሕይወቴ አስጊ ሁኔታ ላይ ስለምገኝ የሚመለከተው አካል ይድረስልኝ” ትላለች፡፡
“አደባባይ የወጣሁት ሕዝቤ እንዲደርስልኝ ነው” ያለችው ገለቴ፣ “ወጥቼ የምወደውን ስፖርት እንኳን እንዳልሠራ ማስፋራራት እየደረሰብኝ ቤት ውስጥ ተዘግቼ ተቀምጫለሁ፤ የአቅሜን ያበረከትኩላት ሀገሬ እና ሕዝብ ያለሁበትን ሁኔታ ይወቅልኝ” ብላለች፡፡
በለሚ ታደሰ ETV

