ሰሞኑን “የኢትዮጵያ መንግስት የአልፋሽቃን ለም መሬት አስመለሰ” የሚል መረጃ በኢትዮጵያ በራሷ “ልጆች” በስፋት እየተዘገበ ነው። መንግስት በደቦና በግል እየቀጠቀጠ ኢትዮጵያና ሕዝቧን ዕረፍት ከሚነሳት ትህነግ ጋር ገጥማ በነበረችበት ወቅት፣ አጋጣምውን ተጠቅሞ የሱዳን መንግስት ለም መሬት መዝረፉ፣ በስፍራው የነበሩ ዜጎችን መግደሉና ንብረታቸውን ማውደሙ አይዘነጋም።
በዛን ወቅት መከላከያን በጦርነት ለመወጠር እነ አቶ ልደቱና ሌሎች “ኢትዮጵያዊ ፊት” ያላቸው ሚዲያዎችና አገልጋዮቻቸው የጋዜጠኛ ልብስ ለብሰው “መንግስት መሬት አስረክቦ ዝም አለ። መሬቱን የማያስመልስ … ” እያሉ በተጠና አካሄድ የመንግስትን ኃይል ለመበታተን ሆን ብለው ይወነጅሉ ነበር።
ዛሬ ደግሞ ሲዳን፣ ሻዕቢያ፣ ግብጽ፣ ትህነግ፣ የምግበ ፋኖ አብረው ኢትዮጵያን ለመውጋት እያሟሟቁ ባለበት ወቅት ለሱዳን ምቹ ሁኔታና ምክኛት ለመስጠት የነሱኑ ጩኸት ማራገብ ምን የሚሉት ኢትዮጵያዊነት ነው? የሚጎዳን ነገር እስከሌለ ድረስ ቢቻል አገርን ወግኖ መቆም ካልሆነ ዝም ማለት እያለ፣ “ኢትዮጵያ ሱዳን ዘልቃ ገባች” በሚል የሱዳንን ትፋት መላስ እንዴት ተብሎ ኢትዮጵያዊ ያሰኛል? ለማንኛውም ከስራ ያለውን ጹህፍ ያንብቡ።
የሱዳን ጉዳይ “ከእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ” እንዳይሆን !
በህወሓት ወረራ ወቅት አገራችን ኢትዮጵያ ችግር ላይ መሆኗን በመረዳት የሱዳን ወታደሮች የኢትዮጵያን ድንብር አልፈው እስከ 50 ኪሎ ሜትር ዘልቀው ወደ ውስጥ በመግባት በምዕራብ ጎንደር እና በወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞኖች በኩል እጅግ ለምና ሰፊ የሆነውን የአልፋሽቃ መሬት በወረራ መያዛቸው እና እስካሁንም ድረስ በእነሱ ስር እንዳለ የሚታወቅ ነው።
ነገርግን “ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮሃል” እንዲሉ ከሰሞኑ Sudan Tribune የተባለውን የሀገሪቱ ተነባቢ ጋዜጣ ጨምሮ አንዳንድ ሚዲያዎች «ሱዳን የውስጥ ችግር ውስጥ መሆኗን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም የኢትዮጵያ ሚሊሻዎች የሱዳንን መሬት በሀይል እየተቆጣጠሩ ነው» የሚል መሰረተቢስ ክስ እያሰሙ ናቸው።
በእርግጥም ሱዳን ችግር ላይ በመሆኗ እነሱ በችግራችን ጊዜ የሰሩትን ስህተት እኛም በእነሱ ችግር ወቅት አንደግመውም ፤ ጊዜው ይለፍና ችግሩን በሰላማዊ መንገድ በውይይት እልባት እንሰጠዋለን የሚል አቋም በኢትዮጵያ በኩል ስለተወሰደ እንጅ ሱዳን ከልጉዲ (ወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን) እስከ ቋራ ነፍስ ገበያ (ምዕራብ ጎንደር ዞን) የተዘረጋ 300 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የኢትዮጵያ ለም መሬት ወስዳ እንደማትቀር የታወቀ ነው።
ያም ሆኖ ከሻዕቢያ ጋር እየሰራ ያለው ከሱዳን ተፋላሚዎች አንዱ የጀኔራል አብዱል ፋታህ አልቡርሃን ቡድን በሱዳን የእርስበርስ ጦርነት ጉዳይ መሃል ላይ በመሆን የአስታራቂነት ሚና እየተወጣች ያለችውን ኢትዮጵያን ጎትቶ ለማስገባት ከሻዕቢያ ጋር በፈፀመው ያልተቀደሰ ጋብቻ ምክንያት “ውሃ ቀጠነ” አይነት ክስ እያቀረበ ይገኛል።
ይሄው የአልቡርሃን ቡድን የኢትዮጵያን መንግስት በሀይል እናስወግዳለን የሚሉ አማፂያንን በማስታጠቅና በማደራጀትም የሚታወቅ ነው።
ሻዕቢያና ህወሃት ተጣምረው ኢትዮጵያን እንወጋለን በሚሉበት በዚህ ወቅት የሱዳኑ የአልቡርሃን ቡድን ይሄንን የበሬ ወለድ ክስ ማንሳቱ ትርጉሙ ግልጽ ነው።
በግብፅ ሁለንተናዊ ድጋፍ ፀረ ኢትዮጵያ እንቅስቃሴ ውስጥ ካሉት ሀይሎች ጋር በይፋ መሰለፉን እየነገረን ነው።
የሆነው ሆኖ ጦርነት የመጀመሪያ ምርጫ ባይሆንምና ከጥቅሙ ጉዳቱ የሚያመዝን ቢሆንም በአስገዳጅ ሁኔታ ምስራቅ አፍሪካ ቀጠና ላይ እንድህ አይነት ባለ ብዙ ተዋናይ ጦርነት ከተቀሰቀሰ “ማን ከማን ጋር ለምን” ይሰለፋል? የሚለውን መገምገም አስፈላጊ ነው።
አያድርገውና ጦርነቱ ከተጀመረ ፦ ኤርትራ ፣ ህወሓት ፣ የምግበይ ፋኖዎች ፣ ሱዳን (የአልቡርሃን ቡድን) ፣ ግብፅ ፣ ኢራን
በአንድ ወገን የሚሰለፉ ሲሆን ኢትዮጵያ ፣ የተባበሩት አረብ ኢምሬትስ፣ ቻድ ፣ አሜሪካ ፣ እስራኤል ፣ ሱዳን (የጀኔራል ሀምዳን ዳጋሎ ቡድን) በሌላ ወገን በቀጥታና በተዘዋዋሪ የጦርነቱ ተዋናዮች የመሆን እድላቸው ከፍ ያለ ነው።
እንደዚህ ከሆነ ደግሞ የጦርነቱ ውጤት ምን ሊሆን እንደሚችል ለመገመት የጦር ሳይንቲስት መሆንን አይጠይቅም።
- ሻዕቢያ እና ህወሃት የተባሉ ፀረ ኢትዮጵያ ሀይሎች ከምድረ ገፅ ይጠፋሉ።
- ኢትዮጵያ የአሰብ ወደቧን ከአስርት አመታት በኋላ ድጋሚ የማግኘት የሀይልና የአመክንዮ የበላይነት ትወስዳለች።
- በኤርትራና ሱዳን አዳድስ መንግስታት እውን ይሆናሉ።
- በጦርነት እና ግጭት የሚታወቀው ምስራቅ አፍሪካ ምናልባትም ሁለቱ አረሞች [ሻዕቢያ እና ህወሓት] ከተነቀሉ በኋላ አድስ የልማትና የሰላም ቀጠና ሆኖ ብቅ ይላል።
- የየመኑ የሁቲ ቡድን ህልውናው ያክትማል።
ኤርትራ እና ጅቡቲ ከኢትዮጵያ ጋር ኮንፌደሬት ሊያደርጉ ይችላሉ…..ወዘተ ብዙ ብዙ ነገሮች ይቀየራሉ ማለት ነው።
Daniel Tilahun Tadesseን ሰኔ 29/2017 ዓ.ም ጋይንት ፤ ጎንደር በጌምድር
ይህ ነጻ አሳብ ነው

