“…. ኤርትራም እጇን አጣጥፋ አልተቀመጠችም። ከተለያዩ ቡድኖች ጋር ግንኙነት እየፈጠሩ እንደሆነ መረጃ አለኝ። በከፊል በትግራይ ግንኙነት እየፈጠሩ ነው፤. . . በአማራም ከፋኖዎች ጋር እንዲሁ ግንኙነት አላቸው” ሲሉ አምባሳደር ኃይሌ መንቆሪዎስ ተናገሩ።
የኤርትራ ተወላጅነት ያላቸው አምባሳደር ኃይሌ መንቆሪዎስ ይህ ያሉት ለቢቢሲ ትግርኛ ነው። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፖለቲካ ጉዳዮች ምክትል ዋና ፀሐፊ አምባሳደር ኃይሌ መንቆሪዎስ ኤርትራ እና ኢትዮጵያ ወደ ጦርነት ከገቡ ሁለቱንም አገራት የሚያወድም እንደሚሆን ማስጠንቀቃቸውም ተመልክቷል።
ጦርነቱ አይመጣም ብሎ ማሰብ እንደማይቻል ያመልከቱት አምባሳደር ኃይሌ “ነገር ግን ምን ዓይነት ጦርነት እንደሚሆን መገመት ይቻላል። ሁለቱም የጠብ አጫሪነት ባህሪ አላቸው፣ ከሕዝብ ፍላጎት ይልቅ ራስን እና ሥልጣንን ማጠናከርን ያስቀድማሉ” ሲሉ የሁለቱን አገራት መሪዎች በእኩል ደረጃ ተችተዋል። ሁለቱንም በተንኳሽነት እኩል ያስቅመጡት አምባሳደሩ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ የባህር በር ጥያቄ ማንሳታቸውን በትንኮሳ ከማንሳታቸው በቀር አሰብን በስም ጠርተው ስለመጠየቃቸው ወይም ስለሶማሊላንድ ውል የኤርትራ ጣልቃ ገብነት ያሉት ነገር የለም። እንዲያብራሩም አልተጠየቁም።
በተባበሩት መንግሥታት በዓለም ዙሪያ የሚነሱ ግጭቶችን ለመፍታት ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶችን የመሩት አምባሳደር ኃይሌ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የባሕር በር ለማግኘት ኃይል የሚጠቀሙ ከሆነ “የዓለም አቀፍ ሕግ ጥሰት ነው የሚሆነው” ሲሉ መላምታቸውን አስቀምጠዋል። እሳቸው ይህን ቢሉም በተደጋጋሚ የኢትዮጵያ መንግስትም ሆነ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በዓለም ዓቀፍ የንግድ ህግ፣ የቢዝነስ አግባብ እንጂ ጦርነት የማንሳት ፍላጎት ኢትዮጵያ እንደሌላት አንስተው በተደጋጋሚ ስለማስታውቃቸው አልገለጹም።
“ለባሕር በር ብሎ ኤርትራን የሚወር ከሆነ፣ ኤርትራ የአፍሪካ ዩክሬን ትሆናለች ማለት ነው። ይህ ደግሞ ግጭቱን የኤርትራ እና የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ቀጠናዊ ያደረገዋል” በማለት አምባሳደር ኃይሌ መንቆሪዎስ ኢትዮጵያን ጠባ ጫሪ የሚያስመስል ማብራሪያ ሰጥተዋል። ይልቁኑም ኢሳያስ በኢትዮጵያ አማጺ እያደራጁ መሆናቸውን፣ ድንበር ጥሰው ገብተው ወታደር ማስፈራቸውን መረጃ እንዳላቸው ከማንሳት በዘለለ አግብብ እንዳልሆነ አንስተው አልተቃወሙም።
ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ወደ ጦርነት የሚገቡ ከሆኑ ሌሎች አገራት ጣልቃ ሊገቡ እንደሚችሉ መላምታቸውን ያኖሩት አምባሳደር ኃይሌ፣ “ሳዑዲ አረቢያ አፍንጫችን ስር ነች ያለቸው። ግብፅ እዚያ አለች…፣ ለማንኛውም ኤርትራ ‘ተወረርኩኝ፤ እርዳታ እሻለሁ’ ካለች፣ ወረራውን ለመቀልበስ ከየትኛውም አገር ድጋፍ የመጠየቅ መብት አላት” ሲሉ ኢትዮጵያ ድንበሯ ተወሮና ሻዕቢያ ታጣቂ እያስለጠነ ወደ ውስጥ ሲያሰርግ በገና ለገና ሌሎች ድጋፍ ሰጪዎች አሉ በሚል ኢትዮጵያ ዝም ማለት እንደሚገባት ለማስጠንቀቅ ሞክረዋል።
አምባሳደሩ አክለውም ኢትዮጵያ የቀይ ባሕር ባለቤት የምትሆን ከሆነ በቀይ ባሕር ቀጣና የሚመጣውን የኃይል ሚዛን ለውጥ ሳዑዲ አረቢያ ጠንቅቃ ታውቃለች በማለት የጂኦፖለቲካውን አሰላለፍ ለውጥ ሲያመላክቱ እስራኤል፣ ፈረንሳይ፣ ሩሲያ፣ አሜሪካና አንዳንድ አረብ አገራት የኢትዮጵያን የባህር በር ጥያቄ መደገፋቸውን ለንጽጽር አላቀረቡም። በጥያቄ ደረጃም አለቀርበላቸውም።
የኢትዮጵያ ወደ ቀይ ባህር መመለስን “ለሳዑዲ ለፍላጎት ጎጂ ይሆናል፤ ስለዚህ ኤርትራን የመደገፍ ፍላጎት አይኖራትም አይባልም” በማለት አምብሳደሩ ኤርትራ ድጋፍ ልታገኝ የምትችልበትን አግባብ አመላክተዋል። አሸባሪዎችን በማሰልጠን፣ ከየመን ሁቲዎች ጋር ግንኙነት እንዳለው በእስራኤል ሚዲያዎች በስፋት እየተወራበት ያለውን ሻዕቢያን ማጥፋት የሚፈልጉ መንግስታት ስለመኖራቸው በገሃድ እንደሚታወቅ የሚጠቅሱ ” አምባሳደሩ የተናገሩት ኢሳያስ የሚያስቡትና ያቅዱት ነው። ይህን ዕቅድ እሳቸው ካሰሉት በላይ የኢትዮጵያ መንግስት ከነኃይል አሰላለፉ ጠንቅቆ ያውቀዋል። ” የሚል አስተያየት ሰጥተዋል።
“አምባሳደር ኃይሌ እንደ ኤርትራ ያለች ትንሽ አገር የአቅም ውስንነት እና አነስተኛ የሕዝብ ቁጥር ስላላት ነገሮች በሰላም እንዲያልቁ መግፋት ነበረባት” ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል። አክለውም “እኔ እንደማስበው ሁለቱም የየራሳቸውን ‘ኅልውና’ እየገፉ ነው። ችግር አያስከትልም ብለን ራስን መሸንገል አያስፈልግም። ነገር ግን መጨረሻው ወዴት እንደሚወስድ ሲታሰብ፣ ሁለቱንም ወደ ግባቸው የሚያደርስ መንገድ አይደለም” ብለዋል።
” በኢትዮጵያ እና በኤርትራ መካከል መቃቃር የመጣው የትግራዩን ደም አፋሳሽ ጦርነት ካስቆመው ከፕሪቶሪያው ስምምነት በኋላ ነው” በሚል ጠቆም ያደረጉት አምባሳደሩ የፕሪቶሪያው ስምምነት ሻዕቢያን ቅር ያሰነበትን መንገድና ምክንያት አላብራሩም። ጥያቄውም አልተነሳላቸውም። ቀተል አድርገውም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ “የባሕር በር ለኢትዮጵያ የኅልውና ጉዳይ ነው” ማለታቸውን ተከትሎ አለመግባባቱ እንደተካረረ አመልክተዋል። መረጃ ያላቸው እንደሚሉት ከሆነ ፕሬዚዳንት ኢሳያስና ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በወደብ አተቃቀምና የባህር በር ጉዳይ ቀደም ሲል ስምምነት ደርሰው ነበር። የፕሪቶሪያው ስምምነት ሲደረግ በማኩረፋቸው ኢሳያስ የተጀመሩትን ንግግሮችና የውል ፕሮፖዛሎች አገዱ።
በአንድ ሉዓላዊ አገር ጉዳይ “ለምን ስምምነት ተደረገ” በሚል ያኮረፉት ኢሳያስ ኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ማንሳቷን እንደ ስጋት ከማየት በዘለለ ሶስማሊላንድ ጋርም ቢሆን ኢትዮጵያ የባህር በር ስምምነት ማድረጓን ተቃውመው ከኢትዮጵያ ተላቶች ጋር በይፋ መሰለፋቸው ኢትዮጵያዊያንን ያሳዘነ ጉዳይ እንደሆነ በተደጋጋሚ መዘገቡ ይታወሳል።
ከስምንት መቶ ሺህ በላይ የኤርትራ ተወላጆችን አቅፋ የያዘችው ኢትዮጵያ በንግድ ውል መሰረት ለኤርትራ ባቀረበችው ጥያቄ መሰረት መግባባት ባይቻል እንኳ፣ከሌሎች አገሮች ጋር የባህር በር ስምምነት እንዳትዋዋል ኢሳያስ የግብጽን አጀንዳ በመሸከም ዘመቻ መክፈታቸው በየትኛውም አመክንዮ እነደማያሳምን፣ ይልቁኑም በኢትዮጵያዊያን ዘንዳ ታሪክ የማይረሳው ጠባሳ እንደሚሆን ምሁራን በተደጋጋሚ እየገለጹ ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የቀደሙ መሪዎች ማድረግ ያልቻሉትን “ኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤት አደርጋታለሁ የሚል ህልም አለው” በሚል የኢትዮጵያውን በግፍ የባህር በር መነጠቅ ወደ ግለሰብ ፍላጎት አሳንሰው አምባሳደሩ ማቀረባቸው “ምን ነካቸው” አስብሏል።
ኢትዮጵያዊያን በራሳቸው ሃብት የገነቡትን የሕዳሴ ግድብ የግለሰብ ሌጋሲ በማውረድ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ህዳሴ የመለስ እንጂ የርሳቸው ሌጋሲ አድርገው ሰላማዩት ወደብ ማስገኘትን ሌጋሲያቸው ለማድረግ እንደሚነቀሳቀሱ በመግለጽ አምባሳደሩ አዲስ ትርክት ፈጥረዋል። አብይ አህመድን “ለኢትዮጵያ ሕዝብ ውርስ እተውለታለሁ ብሎ የሚያስበው፤ የባሕር በር ማስገኘትን ነው። ይሄንን ደግሞ በማንኛውም መንገድ ተግባራዊ ማድረግ ይፈልጋል።” ሲሉ የ130 ሚልዮን ሕዝብን የህልውና ጥያቄ በማቃለል የዝና አስመልስለው አቅርበዋል። ጦርነት እንዳይነሳ ምክር ለግሰው የሕዝብ የዓመታት የባህር በርና የፍትሃዊነት ጥያቄን በቢቢሲ በኩል አሳንሰው አሳይተዋል። ቃለ ምልልሱን የቋጩበት አግባብ ትክክል ቢሆንም እዚህ ላይ ያነሱት አሳብ በብዙዎች አልተወደደላቸውም።
አምባሳደሩ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የባሕር ባር አጀንዳ ካነሱ በኋላ “ኤርትራም እጇን አጣጥፋ አልተቀመጠችም። ከተለያዩ ቡድኖች ጋር ግንኙነት እየፈጠሩ እንደሆነ መረጃ አለኝ። በከፊል በትግራይ ግንኙነት እየፈጠሩ ነው፤. . . በአማራም ከፋኖዎች ጋር እንዲሁ ግንኙነት አላቸው” ብለዋል። ውናዋን ግብጽን እዚህ ጋር ዘለዋታል።
ኤርትራ እጇን አጣጥፋ እንዳልተቀመጠች ካብራሩ በሁዋል አምባሳደር ኃይሌ መንቆሪዎስ ያነሱት ጉዳይ ቢኖር የኢትዮጵያን መዳከም ነው። “ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ሊተማመነባቸው የሚችሉ የአገር ውስጥ ኃይሎች ተከፋፍለዋል” ሲሉ የጀርመን ድምጽ A look at Eritrea’s role as new Tigray war looms in Ethiopia በሚል ርዕስ ከዘገበው ዘገባ ጋር ተመሳሳይ መረጃ ሰጥተዋል። በዘገባው የኤርትራ መንግስት ኢትዮጵያ ውስጥ በየክልሉ ሁከትና ጦርነት እንዲኖር እንደሚሰራና በዚህም ተጠቃሚነቱን እንደሚያሰፋ ተመልክቷል።
“ኢሳይያስ በህወሓት እና በአማራ አማካኝነት በሁሉም በኩል ዐቢይን ለመክበብ እየሞከረ አይደለም ማለት አይቻልም።” በማለት አምባሳደር ኃይሌ መንቆሪዎስ የሻዕቢያን ዕቅድ ግልጥ አድርገው አስታውቀዋል። ይህን ካሉ በሁዋላ ጦርነት ከተጀመረ የሁለቱም አገራት ሕዝብ ከፍተኛ ጉዳት እንደሚያገኛቸው በስጋት መልኩ አቅርበዋል። ጦርነት ከመጣ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን እንጠቀማለን ቢሉም፤ በቀላሉ እና በአጭር ጊዜ ለሁለቱም ድል ይመጣል ብሎ ማመን አንደማይቻልም ጠቁመዋል። ጦርነቱን የሚያረዝመው ኤርትራ ከጀርባዋ አጋዥ ሃይሎች ስላሏት መሆኑን አመልክተዋል።
ከዚህ ሁሉ ማብራሪያ በሁዋላ “አሁን ሁሉም በየፊናው እያጨበጨበ የራሱ መንግሥት ጠበቃ ከመሆን ይልቅ፣ ጦርነቱን ለማስቀረት መሥራት ነው የሚጠቀመው” የሚል ጥሪ አቅርበዋል።
“ጦርነቱ ከተቀሰቀሰ ጉዳቱ ለሁሉም ነው፤ አፍራሽ ነው የሚሆነው፤ ከተቻለ በኢትዮጵያ እና በኤርትራ ውስጥ ያሉ ሕዝቦች እንደ አውሮፓ ወደ አንድ አቅጣጫ ለመጓዝ መሞከር ነው ያለባቸው፤ እንጂ ሌላ ጦርነት መሆን የለበትም።”
ጦርነት ለሁሉም ጥፋት የሚያመጣ መሆኑን የጠቀሱት አምባሳደር ኃይሌ የሁለቱ አገራት ሕዝብ ምሁራን፣ ፓርቲዎች እና ሌሎችም ይህንን ጦርነት ለማስቀረት ጥረት ማድረግ አለባቸው በማለት ጥሪ አቅርበዋል።
“ሕዝቡን ከዚህ ጥፋት ለማዳን የሚፈልግ ካለ ጊዜው አሁን ነው፤ ከቀውሱ በፊት እንጂ ከጦርነቱ መቀስቀስ በኋላ አይደለም። ስለዚህ ይህን ጦርነት ለማስቀረት ሁላችንም ድምጻችንን በማሰማት ኃላፊነታችንን መወጣት አለብን” ብለዋል።
ለፕሬዝዳንት ኢሳያስ እና ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ መልዕክት ሲያስተላልፉም “ለሰላማዊ መፍትሄ፣ ለውይይት ዕድል ስጡ” በማለት ያንዣበበውን የጦርነት ደመና እንዲያስወግዱ ጠይቀዋል።
“በተለይ ለኢሳያስ መልዕክት ብልክ በኤርትራ ውስጥ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመገንባት የታቀደው ተግባራዊ ቢሆን ኖሮ፣ ፓርላማ ቢኖረን ኖሮ፣ በኤርትራ ውስጥ ውይይት እንዲደረግ የሚያስችል ዕድል ቢፈጠር፣ ውይይት የሚፈቅድበት ዕድል ቢፈጠር፣ በዚህ ጉዳይ ላይ እንወያይ ነበር። እና መፍትሄ እናገኝ ነበር” ብለዋል።
ሁለቱ አገራት ወደ ጦርነት የሚገቡ ከሆነ “ሁለቱንም ያጠፋል፣ አቅማቸውን ያዳክማል እና የወደፊት የጋራ ዕጣ ፈንታቸውን ያጠባል” ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
ይህንን ለመከላከል ለሁለቱ አገራት ሕዝብ ጥቅም የሚያስቡ በሙሉ “ይህንን ጦርነት በምንም መልኩ እንዲቃወሙት እመክራለሁ” ብለዋል።
ከሁለት አስርት ዓመታት በፊት በድንበር ይገባኛል ምክንያት ደም አፋሳሽ ጦርነት ያደረጉት ኢትዮጵያ እና ኤርትራ በጠላትነት ሲተያዩ ቆይተው ግንኙነታቸው የተሻሻለው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ነበረ።
ሁለቱ አገራት ግንኙነታቸው ተሻሽሎ በትግራይ በተካሄደው ጦርነት ውስጥ በጋራ የትግራይ ኃይሎችን እስከ ደርሰው የነበረ ቢሆንም ከጦርነቱ ማብቃት በኋላ አለመግባባቶች ተከስተው ግንኙነታቸው ቀስበቅስ ተቀዛቅዞ ወደ ፍጥጫ እያመራ ነው።
ኢትዮጵያ የባሕር በር የማግኘት ፍላጎቷን በይፋ ካሳወቀች በኋላ ሁለቱ አገራት ወደ ግጭት ሊያመሩ ይችላሉ የሚል ስጋት ተፈጥሯል።
የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት የኤርትራ ወታደሮች ትግራይ ውስጥ የያዟቸው ግዛቶች አሉ በማለት እየከሰሱ ሲሆን፣ በሁለቱም በኩል ወታደራዊ ዝግጅቶች እየተካሄዱ መሆናቸው ይነገራል።
ዘገባው ከቢቢሲ ተወስዶ የዳበረ ነው

