የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አህመድ ” በአገር ሽማግሌዎችና የሃይማኖት አባቶች የሚደረግ ምክክርና እርቀ ሰላም ፍሬው ጣፋጭ ነው ” ሲሉ ጦርነትን ለማስቀረት የሚደርገውን ጥረት አደነቁ። ” የፌደራል መንግስት ከህዝብ ፣ ከጊዚያዊ አስተዳደሩና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በፓለቲካ በፀጥታና ኢኮኖሚ እንዲሁም በትግራይ መልሶ ግንባታ ዙሪያ ተቀራርበን እንደምንሰራ ደገመን እረጋግጠንላችኋለን “
ትናንት ሀምሌ 10/2017 ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ ያቀኑት የትግራይ የሃይማኖት አባቶችና የአገር ሸማግሌዎች ዛሬ ሀምሌ 11/2017 ዓ.ም ከኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አህመድ (ዶ/ር) መክረዋል። ይህንኑ አስመልክተው ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ገጻቸው ያሰፈሩትን ትርጉም ቲክቫኽ አስነብቧል።
የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አሕመድ (ዶ/ር) ከትግራይ የሃይማኖት አባቶችና የአገር ሸማግሌዎች ስለተካሄደው የሰላም ውይይት አስመልከተው በማህበራዊ የትስስር ገፃቸው በትግርኛ ባጋሩት መረጃ ” የኢፌዲሪ መንግስት በሽምግልና እና ምክክር ችግሮች እንዲፈቱ ቅድምያ ሰጥቶ እንደሚሰራ በተለያዩ ጊዚያት በተግባር አሳይቷል ” ብለዋል።
” በረጅሙ የአገሪቱ የአገረ መንግስት ስርዓት አገራዊ እርቅ ፣ አገራዊ ምክክር ፣ ፓለቲካዊ ውይይት የሚሉ ማህበራዊ አምዶች በኢትዮጵያ ፓለቲካ ውይይት በይፋ እንዲተገበሩ ያደረገው የአሁኑ መንግስት መሆኑ መካድ የለበትም ” ብለዋል።
” ግጭት ሌላ ግጭት እየወለደ በችግር አዙሪት ከመኖር ያለፈ ሌላ ፋይዳ የለውም ” ያሉት ጠቅላይ ሚንስትሩ ” በውይይትና መግባባት ችግሮቻችን በመፍታት ሰላምን በፅኑ መሰረት እናኑር ” ብለዋል።
” ከተለያዩ የትግራይ የማህበረሰብ ክፍሎች ከተውጣጡ የፐብሊክ ዲፕሎማሲ አካላት ለቀጣይ መደረክ ምቹ መደላድል የሚፈጥር ውይይት አካሂደናል ” ሲሉ ገልጸዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተካሄደው ጥልቅ ውይይት በጥያቄና መልስ የታጀቡ በርካታ ጉዳዮች እንደተነሱ ገልጸዋል።
በፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት አተገባበር ያሉት ተግዳሮቶች እንዴት መታረም አለባቸው ፣ ግጭት ቀስቃሽ የሆኑ ንግግሮች መቆምና መታረም እንዳለባቸው በተለይ የተፈናቃዮችና ትግራይን መልሶ መገንባት ጉዳይ የምክክሩ ዋነኛ ነጥቦች ነበሩ ብለዋል።
የትግራይ ህዝብና ልሂቃን በአገሪቱ ፓለቲካና ኢኮኖሚ በብርቱ ተዋናይ የሚሆኑበት ሁኔታ መፍጠር እጅግ አስፈላጊ እንደሆነና ሌሎች ጉዳዮች ተነስው መግባባት ተደርሶባቸዋል ብለዋል።
” የፌደራል መንግስት ከህዝብ ፣ ከጊዚያዊ አስተዳደሩና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በፓለቲካ በፀጥታና ኢኮኖሚ እንዲሁም በትግራይ መልሶ ግንባታ ዙሪያ ተቀራርበን እንደምንሰራ ደገመን እረጋግጠንላችኋለን ” ብለዋል።
የትግራይ የሃይማኖት አባቶችና የአገር ሸማግሌዎች ትናንት ሀምሌ 10/2017 ዓ.ም በመቐለ ከትግራይ ጊዚያዊ አስተዳደር ፕሬዜዳንት ታደሰ ወረደ (ሌ/ጀነራል) ከተወያዩ በኋላ ወደ አዲስ አበባ በማቅናት ነው ዛሬ ከኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አሕመድ ጋር ውይይት አድርገዋል።
አብይ አሕመድ በቅርቡ በፓርላማ ባደረጉት ንግግር የሃይማኖት አባቶች፣ ዲፕሎማቶች፣ የሚታወቁ አገራት፣ ታላላቆች ሁሉም ጦርነት ከመጀመሩ በፊት የሚችሉትን ሁሉ እንዲያደርጉ ጥሪ ማቅረባቸው አይዘነጋም።

