ተጠርጣሪዎቹ ፋኑኤል ብርሃነ፣ ካህሳይ ተክላይ፣ ፊሊሞን ገ/ማርያም፣ ተክሊት ህሉፍ እና ምህረት ዕድሉ ይባላሉ፣ ፖሊስ ስማቸውን እንጂ ተጠርጣሪዎቹ ከየት ክልል ወይም ጎረቤት አገራ እንደመጡ አላስታወቀም። ይሁንና ዜናው በማህበራዊ ገጽ ይፋ ከሆነ በሁዋላ መነጋገሪያ የሆነው የተጠርጣሪዎቹ ማንነት ጭምር ነው።
የአንድ አመት ከስምንት ወር እድሜ ያለውን ህፃን በማገት ሁለት ሚሊዮን ብር የጠየቁ እና በወንጀሉ ተባብረዋል የተባሉ አራት ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር ማዋሉን ያስታወቀው አዲስ አበባ ፖሊስ ነው።
ወንጀሉ የተፈፀመው ሀምሌ 30 ቀን 2017 ዓ/ም በግምት ከምሽቱ 1፡40 ሰዓት ገደማ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 5 ልዩ ቦታው አፍሪካ ህብረት ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ነው።

ተጠርጣሪዎቹ ፋኑኤል ብርሃነ የተባለን የ1 አመት ከ8 ወር ዕድሜ ያለውን ህፃን ከመኖሪያ ቤቱ በስውር በመውሰድ ወደ ወላጅ አባቱ ስልክ ደውለው ህፃኑን እንዳገቱት በመግለፅ እና ሁለት ሚሊዮን ብር በአካውንት ገቢ እንዲያደርጉ በመጠየቅ በቤተሰብ ላይ ጭንቀትና ድንጋጤን ፈጥረዋል፡፡ አቶ ብርሃነ ገ/ፃዲቅ የተባሉት የህፃኑ ወላጅ አባትም ስለ ሁኔታው በአቅራቢያቸው ለሚገኝ ፖሊስ በወቅቱ አሳውቀዋል።
የህፃኑ መጥፋት ሪፖርት የደረሰው በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ የቄራ አካባቢ ፖሊስ ጣቢያ የምርመራ እና የክትትል ክፍሉ ተቀናጅተው በተደረገ ከፍተኛ ጥረት ካህሳይ ተክላይ የተባለውን እና ከህፃኑ ወላጅ አባት ጋር ዝምድና ያለውን ግለሰብ በቁጥጥር ስር ማዋል ተችሏል፡፡
የወንጀሉ አቀነባባሪ ነው ተብሎ ተጠርጥሮ በተያዘው በካህሳይ ተክላይ ላይ በተከናወነ ምርመራ የማስፋት ስራ በህፃኑ እገታ ከሚገኝ ገንዘብ የጥቅም ተካፋይ ለመሆን በመስማማት ወንጀሉን የተባበሩ ፊሊሞን ገ/ማርያም፣ ተክሊት ህሉፍ እና ምህረት ዕድሉ የተባሉ ተጨማሪ ሶስት ተጠርጣሪዎችም በቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡
እነዚህ ተጠርጣሪዎች የተያዙት ወንጀሉ በተፈፀመ በማግስቱ ሳሪስ አካባቢ በሚገኘው ማራኪ በተባለ ሆቴል ውስጥ አልጋ ክፍል በመከራየት ህፃኑን ይዘው በተሸሸጉበት ወቅት ፖሊስ ባደረገው ክትትል ነው፡፡ በአጠቃላይ በወንጀሉ የተጠረጠሩት አራት ግለሰቦች በአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ ምርመራ እየተጣራባቸው ይገኛል፡፡
ማንም ሰው ወንጀል ፈፅሞ ከህግ ማምለጥ እንደማይችል ከዚህ ወንጀል በመረዳት ህብረተሰቡ አጠራጣሪ ነገር በሚያጋጥመው ወቅት ለፀጥታ አካላት የመጠቆም እና መረጃ የመስጠት ትብብሩን አጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል ሲል የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ ጥሪውን አቅርቧል፡፡
ዘገባ:- ኢንስፔክተር እመቤት ሃብታሙ አዲስ አበባ ፖሊስ

