“የአስረኛ ክፍል ተማሪ ነኝ። ላለፉት ሁለት ዓመታት ወደ ትምህርት ቤት አልሄድኩም። ትምህርት ባይቋረጥ ኖሮ በሚቀጥለው ዓመት ወደ ዩኒቨርሲቲ የምገባበት ጊዜ ነበር። ቤተሰቦቻቸው የገንዘብ አቅም ያላቸው የእድሜ አኩዮቼ ወደ ባሕር ዳር ሄደው ተምረው አሁን ላይ ዩኒቨርሲቲ ሊገቡ ነው። እኔ ግን ሁለት ዓመት እድሜዬን ያለ አግባብ አባከንኩኝ” የሚለው የምሥራቅ ጎጃም ዞን እጁ እነሴ ወረዳ አሚኮ ያነጋገረውና ስለሚፈራ ስሙን የደበቀ ታዳጊ ነው።
ይኸው ታዳጊ አሁንም ትምህርት ሊጀመር በመኾኑ ደስታውንም ገልጿል። ተደርጎ በነበረው በሙከራ የምዝገባ ጊዜ መመዝገቡንም አስታውቋል። እሱ ብቻ ሳይሆን በፍርሃት ስማቸውን እየደበቁ በቤተሰባቸው፣ በልጆቻቸውና በአካባቢው ማህብረሰብ ላይ በግራና በግል የደርሰውን ውድቀት የገለጹ ብዙ ናቸው።
ይህን መስማት በእጅግ ያማል። ማሰብ ለሚችሉ ሁሉ ዕረፍት የሚሰጥም አይደለም። ጉዳዩ ከከርስና ከዩቲዩብ ሽቀላ፣ እንዲሁም በግርድና ከሚገኘው ትራፊ በላይ ነው። የዚህ ልጅ አስተያየት የልብ ውስጥ ለቅሶ ነው። ሲቃ ነው። “እድሜዬን፣ የወደፊት ትልሜን፣ እድሌን ወዘተ ተነጠኩ ” እያለ እያነባ ነው። ማን ይረዳው? እንዲህ ያሉትን ታዳጊዎችና ቤተሰቦቻቸውን ማን ያሳባቸው? እንደዚህ መሰል ሚሊዮን ለጋ ታዳጊዎች ላይ ፈርዶ የ”ሰበር” ዜና ነጋዴ የመሆንን ዝቅጠት በየትኛውም ቋንቋ መግለጽ አይቻልም። በማንኛውም ዓይነት ምሳሌ ማስረዳት አይቻልም። እንደውም እንደ መዓት የሚታይ ነው። በዕርግጥም ማዓት …..
የአማራ ክልል ቢሮ የትምህርት ቢሮ ኀላፊ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ.ር) የ2017 ዓ.ም የትምህርት ዘመን ቅድመ ዝግጅት እና አጀማመርን አስመልክተው ባቀረቡት ሪፖርት “በአማራ ክልል 4 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ቤት አልሄዱም” ብለዋል። ይህን ጉድ፣ ይህን ውድቀት፣ ይህን በታዳጊና ሕጻናት ላይ በግፍ የተወሰደ የጅምላ ግፍ የሚያወራርደው ማን ይሆን?
አሁን እየወጡ ባሉ መረጃዎች ከበፊቱ የተሻለ ቁጥር ያላቸው ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታ ይመለሳሉ ከሚለው ተስፋ ሰጪ ዜና ጎን ለጎን ወላጆች ስጋት ውስጥ መግባታቸው እየተሰማ ነው። አባት ስለልጆቹ አስተያየት ለመስጠት የሚሰጋበትና ስሙን የሚደበቅበት የአማራ ክልል እስከመቼ በዚህ ይቀጥላል?
በአማራ ክልል “ከሰሜኑ ጦርነት ጀምሮ አሁን በክልሉ ባለው ግጭት” ምክንያት ጉዳት የደረሠባቸውን ትምህርት ቤቶች መልሶ ለመገንባት 112 ቢሊየን ብር በላይ እንደሚያስፈልግ የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ ማስታወቁ ይታወሳል። ችግሩ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ቤቶች እንዳይሄዱ ማገድ ብቻ ሳይሆን መማሪያ ስፍራዎችም መውደማቸው ” ምን? ለማን ታስቡ እየተደረገ ነው?” የሚል ጥያቄ ያስነሳል።
የቢሮው ዕቅድ ዝግጅትና ክትትል ዳይሬክተር ዘመነ አበጀ በጦርነቱ እና በአሁኑ ግጭት በርካታ ትምህርት ቤቶች መጎዳታቸውን ሲገልጹ፣ ለአብነት በምሥራቅ ጎጃም ዞን ከ400 በላይ ትምህርት ቤቶች ሙሉ በሙሉ መውደማቸውን ለፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን አስታወቀው ነበር።
ቢሮው ባስጠናው ጥናት መሠረት በአጠቃላይ በክልሉ ጉዳት የደረሰባቸውን ትምህርት ቤቶች ወደ አገልግሎት ለመመለስ ያስገልጋል የተባለው 112 ቢሊየን ብር ትምህርት ቤቶችን ከመገንባትና መጠገን በተጨማሪ ተጓዳኝ የትምህርት ሥራዎችን ለማከናወን የሚውል ነው።
በሰሜኑ ጦርነት 4 ሺህ ትምህርት ቤቶች በአማራ ክልል መውደማቸውን የክልሉ ትምህርት ቢሮ መረጃ ማስታወቁ ይታወሳል። ከዚህ ውስጥ የተጠገኑት ከ10 በመቶ በላይ አለመሆኑም ተገልጿል።
በዚሁ የሰላም ችግር ሳቢያ በ2017 የትምርት ዘመን 40 በመቶ የሚሆኑ ትምህርት ቤቶች ምዝገባ ሳይካሄድ፣ አንድም ትምህርት ቤት ያልተከፈተባቸው 17 ወረዳዎች መኖራቸው የክልሉ የትምህርት ቢሮ ኀላፊ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ.ር) በህዳር ወር መግለጻቸው አይዘነጋም።
ይህንና ሌሎች ሰፊ ጉዶችን የተሸከመው የአማራ ክልል በውስጡ የነገር አገር ተረካቢ የሆኑ ታዳጊዎችን ተስፋ እየመከነም ነው። ታዳጊው እንዳለው እድሚያቸው እየተሰረቀ፣ ተስፋቸው እየጠወለገ፣ ብርሃናቸው እየደበዘዘ፣ ስሜታቸው እየቀዘዘ፣ አስተሳሰባቸው እየተበላሸ ነው። ለዚህ ሁሉ ቀውስ፣ በሚሊዮን ለሚቆጠሩ ታዳጊዎችና ሕጻናት ጉዳት ታሪክ ማንን ይጠይቅ ይሆን?
በትምህርት ብቻ ሳይሆን አምቡላንስ የሚነድበት አማራ ክልል፣ የጤና ጣቢያ የሚወድመበት፣ ማዳበሪያ አርሶ አደር ጋር እንዳይደርስ የሚደረግበት፣ የሕዝብ የገንዘብ ተቋማትና የልማት ድርጅቶች የሚዘረፉበት አማራ ክልል ከዚህ ችግር ቢላቀቅ እንኳስን እንዴት ዳግም ተመልሶ ያገግም ይሆን?
በምሥራቅ ጎጃም ዞን በርካታ ትምህርት ቤቶች ላለፉት ሁለት ዓመታት አላስተማሩም። ብዛት ያላቸው ተማሪዎችም ከትምህርት ገበታ ውጭ ኾነው ቆይተዋል፡፡ በ2018 የትምህርት ዘመን በሁሉም ትምህርት ቤቶች ትምህርት ለማስጀመር የክረምት የቅድመ ዝግጅት ሥራ እየተሠራ ነው ፡፡ ቤተሰብ “መጨረሻውን ያሳምረው” እያለ ነው። ተማሪዎችም በቁጭት የሚከፈትበትን ቀን እየጠበቁ ነው። ትምህርት ለማስጀመር ከመጋቢት ወር ጀምሮ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ከዞን እስከ ቀበሌ ድረስ ውይይት ሲካሄድ ቆይቶ ነው ምዝገባ የተጀመረው። ይህ ነበር “ሰበር ዜና” ግን ትርፍ የለውም !!
የተጠቀምነው የጥር ወር ዳታን ጭምር ነው!!

