ከኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ወለጋ ዞን ኪረሙ ወረዳ እና ከምዕራብ ሸዋ ዞን ዳኖ ወረዳ ተፈናቅለው በአማራ ክልል ጃራ እና ቻይና መጠለያ ጣቢያዎች ተጠልለው የሚገኙ ተፈናቃዮች “ተገደን ጥለነው ለመጣነው መሬት” “ግብር ካልከፈላችሁ ይወረሳል” መባላቸውን አስታወቁ። አስተዳደሩ መሬት ይወረሳል እንዳልተባለ ገልጸዋል።
ለደህንነታቸው በመስጋት ስማቸውን እንዳንጠቅስ የጠየቁ በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን ጃራ መጠለያ ጣቢያ የሚገኙ አንድ ተፈናቃይ ህዳር 9 ቀን 2015 ዓ.ም ከምስራቅ ወለጋ ዞን ኪረሙ ወረዳ ተከስቶ የነበረውን ግጭት ተከትሎ ቤት ንብረታቸውን ጥለው መውጣታቸውን አስታውሰዋል።
በወቅቱ ሸቀጥ በጅምላ በማከፋፈል ንግድ ስራ ሲተዳደሩ እንደነበረ የሚገልጹት ተፈናቃዩ፤ የንግድ እቃዎቻቸው ተዘርፎ፤ ቤታቸው ተቃጥሎ እና የተረፈው ንብረቶቻቸው ተወስደውባቸው በባዶ እጃቸው ቀዬአቸውን ለቀው መውጣታቸውን ይናገራሉ።
ይሁን እንጂ አሁን ላይ ከመጠለያ ጣቢያው ተመልሰው ኪረሙ ወረዳ የገቡ ነዋሪዎች ለመሬት ግብር መክፈላቸውን ገልጸው፤ ነዋሪዎቹ ለአከባቢው አስተዳዳሪዎች “ያልተመለሱት እና ተፈናቅለው በየመጠለያ የሚገኙ ሰዎችስ መክፈል ይኖርባቸዋል ወይ ብለው ሲጠይቁ ከአከባቢው አስተዳዳሪዎች በኩል መክፈል እንዳለባቸው የሚገልጽ ምላሽ እንዳገኙ እና ይሄንኑ ለሚቀርቡት ሰው እየደወሉ እንዲናገሩ መደረጉን” ጠቁመዋል።
ይህን ተከትሎም እዚያው [ኪረሙ] ካለ ሰው የመሬት ግብር እንዲከፍሉ፣ የማይከፍሉ ከሆነ ግን መሬታቸው “ወደ መሬት ባንክ እንደሚገባ” እንደተነገራቸው የሚገልጹት ተፈናቃዩ፤ በሚያዚያ ወር ከተሰጣቸው 7ሺህ ብር የእርዳታ ገንዘብ ላይ ቆርጠው 4100 ብር መክፈላቸውን ተናግረዋል።
የአምስት ልጆች አባት መሆናቸውን የሚገልጹት እኚሁ ግለሰብ አሁን ላይ በጃራ መጠለያ ጣቢያ ሶስት ዓመት ሊሞላቸው መቃረቡን እና ኑሮ እጅጉን አስቸጋሪ እንደሆነባቸው ጠቅሰው አከባቢው ቢረጋጋ ወደ ቀዬአቸው መመለስ እንደሚፈልጉ ገልጸዋል።
“እዚህ መጠለያ ከመጣን ሶስት አመት ሊሞላን ነው፤ መንግስት ምን እያሰበ እንዳለ ግራ ገብቶናል። ስንት መማር የሚችሉ ልጆች ያለ ትምህርት በመጠለያ ለማሳለፍ ተገደዋል። ይሄ ሀገሪቱን ወደ ውድቀት ነው ሚወስደው” ብለዋል።
ሌላኛው በተመሳሳይ ከምስራቅ ወለጋ ዞን ኪረሙ ወረዳ ተፈናቅለው በጃራ መጠለያ ተጠልለው የሚገኙ አንድ ስሜ ባይጠቀስ ያሉ ግለሰብ፤ የአጎታቸው ልጅ ኪረሙ እንዳለ ጠቁመው “መሬቱ ይወሰዳል” የሚል ማስፈራሪያ ሲበረታ 2425 ብር እንደከፈለ ለአዲስ ስታንዳርድ ገልጸዋል።
“ለራሴ ተፈናቅዬ ያለሁኝ እንዴት ትከፍላለህ ብዬ ተቆጣሁት [የአጎታቸውን ልጅ]” ያሉት ተፈናቃዩ ከቤት ግብር በተጨማሪም በእጅ ስልካቸው ላይ ተደውሎላቸው የመብራት እና የውሃ ታሪፍ ክፍያ እንዲከፍሉ እንደተነገራቸው አስረድተዋል። “እኔ እንደሆንኩ እንደምታዩኝ ተፈናቅዬ ነው ያለሁት፤ ውሰዱት እንጂ መክፈል አልችልም” የሚል ምላሽ መስጠታቸውን ተከትሎ የውሃ ቆጣሪው እንደተቆረጠባቸውም ገልጸዋል።
በ2015 ዓ.ም ህዳር ወር ላይ ተፈጥሮ በነበረው ሁከት ቀዬአቸውን ለቀው መውጣታቸውን የሚገልጹት ግለሰቡ “የእርሻ መሬት፣ ወፍጮ ቤት፣ ከብቶችም ነበሩኝ። ይሄ ሁሉ እንደማይሆን ሆኗል። ምንም ሳልይዝ ነው የወጣሁት” ብለዋል።
ያለ ፈቃዳቸውም ቢሆን በአጎታቸው ልጅ በኩል የመሬት ግብሩ ቢከፈልላቸውም “አሁን ላይ ሌላ ሰው ነው መሬቴን እያረሰ ያለው” ሲሉ ሁኔታውን አስረድተዋል።
ሌላኛው ከአዲስ ስታንዳርድ ጋር ቆይታ ያደረጉት ከኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ዳኖ ወረዳ ተፈናቅለው በደብረ ብርሃን ከተማ ቻይና ካምፕ ተጠልለው የሚገኙ ተፈናቃይ በበኩላቸው፤ ከቀበሌ ኃላፊዎች ተደውሎላቸው “የመሬት ግብር የማይከፍሉ ከሆነ ንብረታቸው እንደሚወረስባቸው እና ወደ መሬት አስተዳደር እንደሚገባ” እንደተነገራቸው ገልጸዋል።
በጥቅምት ወር 2013 ዓ.ም ተፈናቅለው መጠለያ ጣቢያው መግባታቸውን የሚያስታውሱት ግለሰቡ ጥለውት ለተፈናቀሉት መሬት የአምስት አመት 8ሺህ ብር እንዲከፍሉ መጠየቃቸውን አመልክተዋል።
“አራት አመት ሙሉ የተጎዳ እና በእርዳታ ያለ፣ ዛሬ ነገ ልጆቼ ይሞታሉ በሚል ስጋት እየኖረ ያለ ህዝብ ነው ያለው። ጥያቄያችን ቦታችን ተመልሰን እያለማን ለመንግሥት ግብር እንክፈል የሚል ነበር። እንኳን ያ ሊሆን በዘዴ እኛን ከቦታው የማስለቀቅ ይመስላል የተያዘው” ብለዋል።
አያይዘውም ሰባት ልጆች እንዳሏቸው ተናግረው “ዱቄት እየለመንን እየኖርን ግብር መክፈል እንዴት እንችላለን?” ሲሉ ጠይቀዋል።
ተፈናቃዮቹ ባነሱት ቅሬታ ላይ ለአዲስ ስንዳርድ ጋር ምላሽ የሰጡት የኪረሙ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አለባቸው ዋይሳ በበኩላቸው፤ “አንድ ሰው የመሬት ባለቤትነቱን ለማረጋገጥ ግብር መክፈል አለበት” ሲሉ ገልጸው፤ “ይህ ለእነሱም ቢሆን ይጠቅማል” ብለዋል።
“ነገር ግን መሬት ይወረሳል አልተባለም” ሲሉ ገልጸው፤ በተጨማሪም “የግብር ክፍያው ከቀዬአቸው ተፈናቅለው በመጠለያ ተጠልለው ለሚገኙ ሰዎች አልተጠየቀም እንደዛ የሚል አመራር ካለ እናጣራለን” ማለታቸውን የዘገበው አዲስ ስታንዳርድ ነው።


