ኢትዮሪቪው፦ የኢትዮጵያን በኢኮኖሚው ዘርፍ የጀመረችውን ጉዞ ዘላቂ ለማድረግ ወታደራዊ አቅሟን መገንባትና በብቃት ማደራጀት እንደሚያስፈልግ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ አስታወቁ። ይህ ካልሆነ የተገኙ ኢኮኖሚያዊ ለውጦችንና እድገትን ማስጠበቅ እንደማይቻልም አመላክተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን ያሉት ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ ገዢነታቸው ከተነሱት አቶ ማም ምህረቱ በተጨማሪ ከሌሎች የስራ ባልደረቦቻቸውና ካቢኔዎች ጋር በኤሮ አባይ የድሮን ማምረቻ ጉብኝት ባደረጉት ወቅት ነው። በጉብኝታቸው ወቅት እንዳብራሩት ኢትዮጵያ ለንግድ፣ ለቅኝት እና ለዘመቻ የሚሆኑ በርካታ ድሮኖችን እያመረተች ነው።
አንድን ሀገር ከሚያቆሙ ምሰሶዎች መካከል አንደኛው የኢኮኖሚ ለውጥ መሆኑን በማመልከት ኢትዮጵያ በዚህ ከፍተኛ ውጤት እያስመዘገበች መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስታውቀዋል።

በኢኮኖሚ ሪፎርሙ ኢትዮጵያ የኢኮኖሚ እመርታ እያስመዘገቡ ካሉ በቁጥር የሚጠቀሱ አገራት መካከል አንዷ እንደሆነች ያመለከቱት አብይ አሕመድ፣ “በትክክለኛ ጎዳና ላይ የሚገኘውን የኢኮኖሚ እድገት በወታደራዊ አቅም መደገፍ ብልጽግናን ለማረጋገጥ ወሳኝ ነው” ብለዋል። ህንድን እንደ ምሳሌ በማንሳት የጉዳዩን ተያያዥነት አመላክተዋል።
በተደጋጋሚ ሲናገሩ እንደሚሰማው የኢትዮጵያ ብልጽግና እውን የሚሆን፣ የኢትዮጵያ መለወጥ የማያጠራጥር ሀቅ መሆኑን የጠቆሙት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በኢኮኖሚ የተጀመሩ ጉዞዎች በወታደራዊ አቅም እያስደገፉ መሄድ እንደሚያስፈልግ አጽንዖት ሰጥተዋል። የአንድ ሀገር እድገት የሚለካው በገንዘብ ብቻ ሳይሆን ባላት ወታደራዊ አቅምም ጭምር እንደሆነም አስታውቀዋል።
ትናንት ከዘመን ወደኋላ መቅረት የከፋ ዋጋ አስከፍሎናል። የአድዋ ድል በሁለተኛው የፋሽስት ወረራ ያልተደገመው ዘመኑን መዋጀት ተስኖን ነው። ዛሬ የትናንት ክፍተትን እየሞላን፣ ዛሬን እየሰራን ነገን ለመጨበጥ እንተጋለን።
ኢትዮጵያ ለመበልጸግ የሚያስችል ከፍተኛ አቅም ያላት ሀገር መሆኗን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ ቴክኖሎጂ፣ ቱሪዝም እና ማዕድን እየተገኘ ያለውን ውጤት እና እድገት በወታደራዊ አቅም መጠናከር እንዳለበት አመልክተዋል።
ይህን ካሉ በሁዋላ የዛሬውም ጉብኝት ኢትዮጵያ ከኢኮኖሚ እድገቷ ጎን ለጎን እየገነባች ያለውን ወታደራዊ አቅም የሚያሳይ መሆኑን ነው ገልጸዋል።
በኤሮ አባይ በቀላሉ የተለያዩ መገልገያዎችን ይዘው ለመንቀሳቀስ የሚሆኑ የቅኝት ድሮኖች እና ለንግድ የሚውሉ ድሮኖች እየተመረቱ መሆኑን አብራረተዋል። ድሮን በተለያዩ የአገሪቱ ተቋማት እየተመረተ እንደሚገኝም አክለው ተናግረዋል።
የራስን ፍላጎት ከማሟላት አልፎ ለገበያ ማቅረብ የሚቻልበት ደረጃ መደረሱን ያመልከቱት አብይ አሕመድ፣ አጥፍቶ ጠፊ ድሮኖች የጠላትን ኃይል ባለበት የሚያመክኑ መሆኑን፣ የስለላ ድሮኖች ደግሞ የጠላትን ክምችትና ስምሪት፣ እንዲሁም እንቅስቃሴ በመከታተል የተጠና ኦፕሬሽን የሚያሳልጡና የሚወስዱ ቁልፍ የወታደራዊ አቅም መሆናቸውን አብራርተዋል።
ኢትዮጵያ ከዓመታት በፊት ድሮን መታጠቅ ሳይሆን የመግዛት ፈተና እንደነበረባት ቀደም ሲል ትጥቅ ለመግዛትና ራስን ለመከላከል የነበረውን ፈተና በማስታወስ የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሁን ገዝቶ ከመጠቀም አልፎ ማምረት መቻሉን ትልቅ እመርታ እነሆነ ጠቁመዋል።
ወታደራዊ አቅም የኢትዮጵያን ህልውና እና ሉዓላዊነት የሚገዳደር ኃይል ሲመጣ ቴክኖሎጂውን በመጠቀም የተጀመረውን ብልጽግና ለማስጠበቅ የሚያስችል መሳሪያ እንደሆነም አብይ አሕመድ በገለጻቸው ይፋ አድርገዋል።
የኢኮኖሚ እና ወታደራዊ እድገት ሲረጋገጥ የኢትዮጵያን ባህል፣ ታሪክ እና መልክዐ ምድራዊ ገጽታ በኪነጥበብ ስራዎች በማጉላት ሁለንተናዊ ብልጽግናን ማረጋገጥ እንደሚቻል ተናግረዋል።
“ኢትዮጵያ ድህነት እና ችግር የማይመጥናት ሀገር ናት” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቴክኖሎጂው ረገድ የተጀመረው አጠቃላይ ስራ የመወዳደር አቅም ያላት ሀገር ለመገንባት እና ብልጽግናን እውን ለማድረግ እንደሚያስችል አመልክተዋል።
“ኢትዮጵያ እያመረተቻቸው ያሉ ድሮኖች ሉዐላዊነቷን በማስጠበቅ፤ የተጀመረውን ብልጽግና ማስቀጠል የሚያስችሉ ናቸው” የተባሉት ድሮኖች በኢትዮጵያ መመረታቸው ከወራት በፊይ ይፋ መሆኑን ተከትሎ የምዕራብ አፍሪካ አገሮች የግዢ ጥያቄ ማቅረባቸው አይዘነጋም።
በቅርቡ በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት የተዘጋጀው የድሮን ትርዒት፤ በማምረቻው በተመረቱ የሰው አልባ አውሮፕላኖች የተከናወነ ድንቅ ጥበብ እንደነበር የሚታወስ ነው።
ሁሉም የኢትዮጵያዊ የኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ብልጽግና የሚያረጋገጡ ስራዎች ላይ ርብርብ እንዲያደርግ ጠቅላይ ሚኒስትሩ እግረ መንገዳቸውን ጥሪ አቅርበዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በፍጥነት፣ በጥራትና በከፍታ የኢትዮጵያን ብልጽግፍና ለማሳካት መሰራት እንዳስለበት ወደ ስልታን ከመጡበት ጊዜ ጀምሮ በተደጋጋሚ የሚናገሩት መርሃቸው እንደሆነም አየዘነጋም።

