“ዛሬ ግድቡ ሞልቷል። በሙሉ አቅሙ ኃይል እያመረተ ነው። ህልማችን ዕውን ሆኗል። ማንም ሊደግፉት አልፈለጉም። በፖለቲክና በርካታ ጉዳዮች ተተብትቦ ነበር። ነገር ግን ኢትዮጵያዊያን አደረጉት” ይህ እንባን የሚያዋልድ፣ ቁጭትን የሚንድ ንግግር ነው።
“ዛሬ እዚህ ሆነን የምናየው እውነት ከዚህ በፊት የሚሆን አይመስልም ነበር” የሚለው የፔትሮ ሳሊኒ ንግግርና የህዳሴው ግድብ እንዴት ዕውን ሊሆን እንደቻለ ለሚያውቁና ለሚረዱ እጅግ ትርጉም ያለው እንደነበር ስለ ፕሮጀክቱ መረጃ ያላቸው ይናገራሉ።
በ1960ዎቹ ኢትዮጵያ ሲመጡ ጨለማ እንደነበር ያወሱት ሳሊኒ፣ ዛሬ እውን የሆነው የአባይ ግድብ ተሳክቶ ሊታይ የሚችል እንደማይመስል ያስረዱት በብዙ ማብራሪያዎች ላይ ነው።

የጣሊያኑ ሳሊኒ ኩባንያ ስራ አስኪያጅ ፔትሮ ሳሊኒ በየታላቁ ሕዳሴ ግድብ ምርቃት ሥነ ስርአት ላይ ባስተላለፉት መልዕክት “ዛሬ እዚህ ሆነን የምናየው እውነት ከዚህ በፊት የሚሆን አይመስለንም ነበር፤ ይኸው ከ14 ዓመታት በኋላ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እውን ሆኗል” ብለዋል። በፍጹም ኢትዮጵያዊ ስሜት ስኬቱን ሲያጎሉ የነበሩት ሳሊኒ ግድቡን ሲያንቋሽሹና ተልዕኮ ወስደው ሲያሰናክሉ ከነበሩ “ኢትዮጵያዊያን” ከሚባሉት ጋር ሲመዘኑ ምላሹ “ታሪክና ትውልድ ይፍረድ” ከማለት ውጭ ምንም ማለት እንደማይቻል በበዓሉ ላይ የተገኙ ነግረዋናል።
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ብቻ ሳይሆኑ በርካቶች ማንባታቸውን ያወሱት እነዚህ ወገኖች የታላቁ የሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ዋና ስራ አስኪያኪጅ ኢንጂነር ክፍሌ ሆሮ እንዳሉት ተልዕኮ የወሰዱ እስከ 200 ኪሎሜትር ዘልቀው በመግባት ቦንብ ቀብረዋል። የኢትዮጵያ ምርጥ ልጆች በቦንብ ላይ ተረማምደው አምክነዋል። ለኝባታው ምርት የሚመረቱባቸውን ፋብሪካዎች ለማፈንዳት በዙ ተሚክሯል። የግብአት ውጤቶች ወደ ፕሮጀክት እንዳይደርሱ ሲደረግ መስዋዕት ተከፍሏል። ይህ የሆነው በባዕድ ሳይሆን በ”ተገዙ ወገኖቻችን” ነው።
“ግድቡ ዛሬ ላይ በሚፈለገው የውኃ መጠን ሞልቶ፣ ተርባይኖቹም የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጨት ጀምረዋል” ያሉት ፔትሮ፣ “ሁሉም ነገር በትክክል እየሠራ ነው፤ ይህ እጅግ አስደናቂ ነው፤ እጅግ ደስ የሚል ነገር ነው” ማለታቸው ትርጉም የሚሰጠው ግድቡ በላብ፣ በደም፣ በሕይወት፣ በአገር ሐብትና የህዝብ ገንዘብ መገንባቱንና በኝባታው ሂደት የታለፈበትን አስቸጋሪ ጎዳና በወጉ መረዳት ሲቻል ብቻ ነው።
“ይህ ለእኔ እና ለኢትዮጵያ እውን የሆነ ሕልም ነው፤ ዛሬ ምን ያህል እንደኮራሁ ልነግራችሁ እወዳለሁ፤ ልቤ የኢትዮጵያውንን አንድነት እየዘመረች ነው” ሲሉም ሳሊኒ የተሰማቸውን ጥልቅ ስሜት የገለጹት እንዲሁ ውዳሴ ለማሳመር የማይሆነውም በዚሁ ምክንያት ነው።
የጣሊያን ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጂያ ሜሎኒ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና ለመንግሥታቸው የደስታ መግለጫ መልዕክት መላካቸውንም ፔትሮ ሳሊኒ አስታውቀው ስለ ኃይልና ነገ አያይዘው ንግግር ሲያደርጉ፣ የኢትዮጵያንም ፍትሃዊነት አስረግጠው በማስረጃ አመልክተዋል።
ከታላቁ የሕዳሴ ግድብ የሚመነጨው የኤሌትሪክ ኃይል ኢትዮጵያ አሁን ያላትን በሦሰት እጥፍ የሚጨምር መሆኑንም ያስታወሱት ፔትሮ ሳሊኒ ከሕዳሴ ግድብ ጋር የሚስተካከል የኒውክሌር ማበልጸጊያ ሲጨመር ደግሞ ኢትዮጵያ ለጎረቤት ሀገራት የኤሌክትሪክ ኃይል በመሸጥ ወዳጅነታቸውን የበለጠ ለማጠናከር እና ቀጣናዊ ልማትን ለማፋጠን ያገለግላል ብለዋል። በዚህ ድንቅ ሥራ ከጅማሮው እስከ ፍፃሜው ሂደት አሻራቸውን ላሳረፉ ሁሉም ሠራተኞች ምስጋና አቅርበዋል።
በዚህ ግድብ ግንባታ ሥራ ላይ እየተሳተፉ በነበረ ወቅት በተለያዩ አደጋዎች ሕይወታቸውን ላጡ ሠራተኞች ክብር እንደሚሰጡ እና በኅሊና እንደሚያስቧቸው ሳሊኒ ሲናገሩ የተከፈለው ዋጋ ለገባቸውና በቅርብ ለሚያዉቁ እንባቸው ማቆሚያ አልነበረውም። “ከጅምሩ ለኢትዮጵያ ውድቀት በኢትዮጵያዊ ካባ የሚጫወቱና ዘረኝነት ያጠመቃቸው ክፍሎች ሲጀመር የተከፈለው ዋጋ ስለማይገባቸው አያለቅሱም። የሚያለቅሱ ዜጎች ሲያዩም ለመቀበል ይቸገራሉ። በተልዕኳቸው መጠን በዕንባ ሊሳለቁ ይታያሉ” ሲሉ እዛው ግድቡ ላይ ዕድሚያቸውን የገፉ ይናገራሉ። እነዚህ ወገኖች ግድቡ እውን እንዲሆን የተከፈለውን ዋጋ አንድ ቀን በዝርዝር ሲቀርብና በታሪክ ለትውልድ ሲሰነድ እነዚህ ወገኖችም የህዳሴው ታሪክ የተቃራኒው ወገን ምድብተኞች እንደሚሆኑ አመልክተዋል።
“ታላቁ የሕዳሴ ግድብን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ነባራዊ ሁኔታዎችን በመጋፈጥ ዛሬ ለምናየው ፍሬ አድርሰውታል” ሲሉ ፔትሮ ሳሊኒ ምስክረነታቸውን ለታሪክ አኑረዋል።
ኢንጂነር ክፍሌ ሆሮ ” ፕሮጀክቱ ልምድ በሌለው ኮንትራክተር እንዲሰራ በመወሰኑ መንግስት 450 ሚሊየን ዩሮ ካሳ ከፍሏል” ሲሉ የሰጡትን ዝርዝር መረጃ የሰሙ ዜጎች ለውጡ ባይመጣ ኖሮ ፕሮጀክቱ በተያዘለት ሰባት ዓመታት ቀርቶ ዕድሜ ልኩን ሊጠናቀቅ እንደማይችል እየገለጹ ነው። በተመሳሳይ ፕሮጀክት ዓይነት ድርሽ ብለው የማያውቁ ባለሙያዎች ተመድበውበት በነበረበት ወቅት ግብጽ ግድቡ እንደማይጠናቀቅ አውቃ ዝም ብላ ተቀምጣ እንደነበር ያስታወሱት ኢንጂነሩ ከሪፎርሙ በሁዋላ ግድቡ በወጉ መሰራት ሲጀመር ግብጽ በተለያየ መንገድ ስትገዳደር እንደነበር አመልክተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ “የተደረገለንን ስለማውቅ ፈጣሪዬን ማመስገን እፈልጋለሁ” በማለት ከዓመት በፊት መናገራቸው የዚሁ ሚስጢር እንደሆነ የገለጸልን አንድ ሰራተኛ፣ የሕዳሴ ግድብ ብዙ ዋጋ የተከፈለበት እንደሆነ ያስረዳል። እያያቸው የተሰናበታቸው የስራ ባልደረቦቹ መኖራቸውንም ጠቁሟል።
“ይህ ግድብ እንዲገነባ ማንም አልፈለገም ነበር፤ ማንም የፋይናንስ ድጋፍ አላደረገለትም፤ በርካታ የፖለቲካ ችግሮችም ነበሩ፤ ቀላል ውሳኔዎች አልነበሩም ያሉት ፔትሮ፣ የኢትዮጵያን ባህሪ ግን በፈተናዎች እና በተግዳሮቶች መጠንከር ነው፤ ኢትዮጵያውያን ፈተናዎችን አይፈሩም” ሲሉ ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል።
“ኢትዮጵያውያን ፅኑ ናቸው፤ ተገዳዳሪ ወይም ጠላት ሲያጋጥማቸው አቅማቸውን በእጥፍ በማባዛት ማሸነፍ ይችሉበታል” ሲሉም ሳሊኒ የኢትዮጵያዊያንን አልበገርም ባይነት አጉልተዋል። እሳቸው እንዳሉት ጥቂት ባንዳዎች ቢኖሩም አብዛኞች በአገራቸው ስለማይደራደሩ ሁሉም በድል ተጠናቋል።
“ኢትዮጵያውያን ለማንም አይንበረከኩም፤ ያመኑበትን እና የፈለጉትን ነገር ከማድረግም ወደ ኋላ አይመለሱም፤ ለዚያም ነው ኢትዮጵያ ሁሉንም ተቃውሞ እና አስቸጋሪ ሁኔታዎችን አልፈው ይህንን ፕሮጀክት ያሳኩት” ብለዋል።
መጀመሪያ ተቃውሞ እና ፍራቻም ነበር፤ አሁን የሕዳሴ ግድብ ውኃን የሚይዘው ንጋት ሐይቅም ሙሉ ለሙሉ ሞልቷል ያሉት ፔትሮ ሳሊኒ፣ በፊት ሲፈራ እንደነበረው ለታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ምንም ስጋት አለመሆኑን አስመስክሯል ሲሉ ገልጸዋል።
ቤተሰባቸው ከቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ ጊዜ ጀምሮ ከኢትዮጵያ ጋር ጥብቅ ቁርኝት እንዳለው ተናግረው ከለገ ዳዲ ግድብ እስከ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በመሥራት ለኢትዮጵያ የንፁህ መጠጥ ውኃ እና የኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎት መሳካት ሚና መወጣቸውን ጠቁመዋል። ዛሬ በሕዳሴ ግድብ ምርቃት ላይ የጋበዙት ልጃቸውም ከኢትዮጵያ ጋር መሥራት እንዲቀጥሉም ኃላፊነት ሰጥተዋቸዋል።

“ስለ ኢትዮጵያ ወርቅ አንብቤ ነበር፤ ይህ ወርቅ ግን እንደምናስበው ውዱ ብረት አይደለም፤ ይህ የኢትዮጵያ ወርቅ ውኃዋ ነው” በማለት ሳሊኒ ፔትሮ ተናግረዋል።
የቀጣዩ ዘመን ወርቅ ውሃ በመሆኑ ኢትዮጵያ ተጨማሪ ሶስት ግድቦችን ለመገንባት ዝግጅቷን እንዳጠናቀቀች ተሰምቷል። ኢትዮጵያ ማንንም ሳትጎዳ ያላትን የተፈጥሮ ሃብት ለመጠቀም እንደምትሰራ ይፋ አድርጋለች። ግብጽ በበኩሏ የተለመደውን ክሷን በመያዝ ወደ ጸጥታው ምክር ቤት ማምራቷ ተሰምቷል። ሳሊኒ የህዳሴው ግድብ በመገደቡ ግብጽም ሆነች ሱዳን አንድ ሲኒ ውሃ እንዳልጎደለባቸው ደጋግመው ተናግረዋል።
የአባይ ግድብና ኢትዮጵያ ብቻ በዓለም ታሪክ የጸጥታው ምክር ቤት አጀንዳ መሆናቸው ባለፉት ዓመታት እጅግ መነጋገሪያና እንደነበር አይዘናጋም። በሌላም በኩል ግድቡ መሸጡን፣ ለሌላ አካል መተላለፉን፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ክህደት መፈጸሙን የጠቅላይ ሚኒስትሩን ስም በመጥራት ሲዘግቡና አደባባይ ሲተነትኑ የነበሩ ይህ እስከተጻፈ ድረስ ይቅርታ ወይም ማስተባበያ አልሰጡም። ይልቁኑም የግንባታውን ውጣ ውረድ፣ የተከፍለውን መስዋዕትነት እንዲሁም በሁሉም አቅጣጫ ተከፍቶ የነበረውን ጫና በማሰብ አምላካቸውን በዕንባ ያመሰገኑ ላይ ሲዛበቱ ታይተዋል።

