ኢትዮጵያ እና ኬንያ እ.ኤ.አ 1963 ኬንያ ነፃነቷን ባገኘችበት ዓመት December 12, 1963 የጋራ ወታደራዊ ትብብር ሥምምነት የተፈራረሙ ሲሆን ከ 32 ዓመት በኋላ በዛሬው እለት የሁለትዮሽ ወታደራዊ ትብብር ተፈራርመዋል።
የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ክቡር ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ እና የኬንያ መከላከያ ኢታማዦር ሹም ጄነራል ቻርልስ ሙሪዩ ካሃሪሪ በመከላከያ ጠቅላይ መምሪያ የሁለትዮሽ ውይይት ያደረጉ ሲሆን ሁለቱ ተቋማት በጋራ መስራት በሚቻልባቸው መስኮች ወታደራዊ የትብብር ስምምነት (DCA) ተፈራርመዋል ።
የሁለቱ ሃገራት ወታደራዊ የትብብር ስምምነት Defence Cooperation Agreement (DCA) እንደሌሎች ስምምነቶች የሚታይ ስምምነት ሳይሆን ስትራቴጂካዊ በሆኑ ስራዎች ላይ በጋራ መስራት የሚያስችል ሃገሮች በመሃከላቸው ያለው ግንኙነትና መተማመን በሚያድግበት ወቅት የሚፈፀም ነው፡፡
የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ኢትዮጵያ እና ኬንያ የቆዬ ታሪካዊ ግንኙነት እንዳላቸው ተናግረዋል። የኬንያና የኢትዮጵያ መከላከያ ተቋማት በተለያዩ ወታደራዊ መስኮች በትብብር እየሰሩ መምጣታቸውን የገለፁት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ በቀጣይም በጋራ የሚሰሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ነው የገለፁት።
ክቡር ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ከኬንያ መከላከያ ኢታማዦር ሹም ጋር Intelligence sharing ፤ በጋራ ወታደራዊ ልምምድ ፤ በስልጠና በወታደራዊ ኢንዱስትሪ፣ ሽብርተኝነትን በመዋጋት፣ በድንበር ደህንነት እና በሌሎችም ተያያዥነት ባላቸው ወታደራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ተፈራርመናል ብለዋል ።
በተጨማሪም ክቡር ፊልድ ማርሻሉ በስምምነቱ ከሃገራቱ በተጨማሪ በቀጠናው ሰላምና ደህንነት ላይ በጎ ተፅዕኖ የሚፈጥሩ በርካታ ስራዎችን አብረን እንሰራለን ብለዋል፡፡
የኬንያ መከላከያ ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጄኔራል ቻርልስ ሙሪዩ ካሃሪሪ ለዕርሳቸውና ለልዑካን ቡድናቸው ለተደረገላቸው ደማቅና የሞቀ አቀባበል ምስጋና አቅርበዋል።
የኬንያ መከላከያ ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጄኔራል ቻርልስ ሙሪዩ ካሃሪሪ የኢትዮጵያ እና የኬንያ ግንኙነት ከታሪክም ባለፈ በባህል፣ ህዝብ ለህዝብ እና በጅኦግራፊ ላይም የተመሰረተ እንደሆነ ተናግረዋል። ጄኔራል መኮንኑ ጨምረው ኢትዮጵያና ኬንያ ያደረጉት ወታደራዊ ስምምነት ከሁለቱ ሀገራት ባለፈ ለቀጠናው ሰላምና መረጋጋትም የጎላ ፋይዳ እንዳለው ገልፀዋል።
© የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ፌስቡክ

