ኢዜማ እስር ላይ ያሉት የድርጅቱ መሪ ዶክተር ጫኔ ከበደ የድርጅቱን መርህ መጣሳቸውን በይፋ አስታወቀ። ድርጅቱ ባወጣው መግለጫ ከድርጅቱ መርህ ውጭ ባፈነገጠ መልኩ መንቀሳቀስ ኢዜማን እንደማፍረስ እንደሚቆጠር አስታውቋል። የድርጅቱን መርህና አሰራር የዘርዘረው መግለጫ ” የፓርቲያችን ሊቀመንበር ጉዳይም ከዚህ ከላይ ከተገለፀው መርኅ አንጻር የሚታይ ይሆናል ሲል ፓርቲያችን ይገልፃል” ሲል አቋሙን ይፋ አድርጓል። <<…ከሰላማዊ ትግል እና ከዜግነት ፖለቲካ እንቅስቃሴዎች ውጭ ያለን የፖለቲካ እንቅስቃሴ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ መደገፍ፣ የሀሳብም ሆነ የተግባር ተሳትፎም ሆነ ትብብር ማድረግ ከኢዜማዊነት መርኅ ማፈንገጥ መሆኑን ለማስገንዘብ እንወዳለን::>> ብሏል
ኢዜማ ከሰላማዊ የትግል ስልት ውጪ በዘውጌ ብሔርተኝነትም ሆነ አፈሙዝ በታከለበት የትግል መንገድ መንቀሳቀስን ድርጅቱ የቆመበትን መርኅ መቃረን አድርጎ ያየዋል። ማንኛውም የኢዜማ አባል ብሎም ከወረዳ እስከ ብሔራዊ ስራ አስፈፃሚ ድረስ የሚሳተፍ አመራር ከዚህ የድርጅቱ ፅኑ ዕምነት ውጭ የተንቀሳቀሰ እንደሆነ ድርጅቱን ለማፍረስ እንደሚሰራ ተደርጎ እንደሚቆጠር መታወቅ አለበት። ኢዜማ ውስጥ የማይነካም ሆነ የማይተካ አባልም ሆነ አመራር የለም! ስለሆነም ከድርጅቱ ዓላማ እና የትግል መስመር ባፈነገጠ መንገድ በሚንቀሳቀሱ አባላቱ ላይ የፀና አቋም ይይዛል።
ኢዜማ የሊቀመንበሩን መታሰር በተመለከተ የሰጠው መግለጫ
የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) መስከረም 14 ቀን 2016 ዓ.ም የፓርቲያችን ሊቀመንበር ዶ/ር ጫኔ ከበደ በጸጥታ አካላት በቁጥጥር ሥር መዋልን አስመልክቶ በሰጠው መግለጫ ጉዳዩን በጥንቃቄና በትኩረት እንደሚከታተለው፣ መረጃዎችንም በተከታታይ እንደሚያሳውቅ መግለፁ የሚታወስ ነው፡፡
በዚሁ መሠረት የፓርቲያችን ብሔራዊ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይህንኑ ጉዳይ እንዲከታተል የሰየመው ኮሚቴ ባደረገው ማጣራት ዶ/ር ጫኔ ከበደ በቁጥጥር ስር የዋሉት በፓርቲያችን ባላቸው ኃላፊነት ሳይሆን በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መሠረት በኮማንድ ፖስቱ ተጠርጥረው በቁጥጥር ሥር የዋሉ መሆኑን መረጃዎች አግኝተናል፡፡
ይህ መረጃ ከተገኘ በኋላ የብሔራዊ ሥራ አስፈፃሚው ኮሚቴ መስከረም 19 ቀን 2016 ዓ.ም ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ በጉዳዩ ላይ በጥልቀት ተወያይቷል።
በአሁኑ ወቅት ሃገራችንን ሰቅዞ የያዘው የፖለቲካ ውጥረት መነሻ በሁለት እሳቤዎች መካከል በሚደረግ ፅንፍ የረገጠ መካረር መሆኑ እሙን ነው ፡፡ በአንድ በኩል በእውቀት፣ እውነት፣ መርኅ እና ምክንያታዊነት ምሶሶዎች ላይ የተመሠረተው የዜግነት ፓለቲካ፤ ከዚህ በተለየ ደግሞ ተበደልኩ፣ ተገለልኩ፣ የሚገባኝን ያህል የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት እና የፖለቲካ ውክልና ተነፍጎኛል . . . ባህሌን፣ ቋንቋዬን እና ወግ ሥርዓቴን ማሳደግ አልቻልኩም በሚሉ በዘውግ ላይ በተንጠለጠለ ልዩነትን መሰረት ባደረገ የማንነት ፖለቲካ መካከል ሲደረግ የቆየው ግብግብ ከፍተኛ ደረጃ ላይ በመድረሱ ነው ብለን እናምናለን።
በሁለቱ የፖለቲካ መስመሮች መካከል የሚደረገው ትንቅንቅ የሚያስከትለውን የሕይወት እና የንብረት ውድመት፣ በአጠቃላይ ህዝባችንን ከችጋር እና ጉስቁልና በሚያላቅቅ የልማት ሥራ ላይ መዋል ያለበት ውስን የሀገር ኃብት ብክነትን በማስቀረት ከትጥቅ ትግል ይልቅ በመተማመን ላይ የተመሠረተ የሃሳብ ትግል (በሰላማዊ ንግግር ችግሮችን መፍታትን ልንከተለው የሚገባ ብቸኛ የትግል ስልት) እንደሆነ የሚያሳይ አቋማችንን ደግመን ደጋግመን የገለፅነው የአደባባይ ሃቅ ነው።
ኢዜማ በመርኅም ሆነ በተግባር በዜግነት የፖለቲካ አስተሳሰብ እና በፀና የሰላማዊ ትግል መስመር የሚያምን፣ ይህንኑ መርኅ ብቻ ተከትሎ የሚሠራ፣ በማንኛውም ዓይነት ሁኔታ በዘውግ ተኮር የፖለቲካ እንቅስቃሴም ሆነ በኃይል መንግሥታዊ ሥልጣን ለመያዝ በሚደረግ ትግል ውስጥ ፈጽሞ የማይሳተፍ ብቻ ሳይሆን በዚህ መንገድ ተጉዘን ዕረፍት ለናፈቀው ህዝባችን የሰላም አየር ልናመጣለትም ሆነ በዘላቂነት ወደተረጋጋ የፓለቲካ ሥርዓት ልንደርስ እንደማንችል ያለጥርጥር የሚያምን ድርጅት ነው፡፡
ኢዜማ ከሰላማዊ የትግል ስልት ውጪ በዘውጌ ብሔርተኝነትም ሆነ አፈሙዝ በታከለበት የትግል መንገድ መንቀሳቀስን ድርጅቱ የቆመበትን መርኅ መቃረን አድርጎ ያየዋል። ማንኛውም የኢዜማ አባል ብሎም ከወረዳ እስከ ብሔራዊ ስራ አስፈፃሚ ድረስ የሚሳተፍ አመራር ከዚህ የድርጅቱ ፅኑ ዕምነት ውጭ የተንቀሳቀሰ እንደሆነ ድርጅቱን ለማፍረስ እንደሚሰራ ተደርጎ እንደሚቆጠር መታወቅ አለበት። ኢዜማ ውስጥ የማይነካም ሆነ የማይተካ አባልም ሆነ አመራር የለም! ስለሆነም ከድርጅቱ ዓላማ እና የትግል መስመር ባፈነገጠ መንገድ በሚንቀሳቀሱ አባላቱ ላይ የፀና አቋም ይይዛል።
ኢዜማዊነት በምንም መንገድ ሁለት የማይታረቁ ሃሳቦችን እያጣቀሱ መሄድን የማይፈቀድ እንደሆነ መላው የድርጅታችን አባላት፤ እንደዚሁም በክብር፣ በነፃነት እና በእኩልነት የመኖር ዋስትና እንዲረጋገጥለት ዘወትር የምንታገልለት መላው የኢትዮጰያ ህዝብ እንዲያውቅልን እንፈልጋለን።
ሀገራችን ከገባችበት የፖለቲካ ምስቅልቅል ደረጃ በደረጃ ልትላቀቅ የምትችለው በፖለቲካ ምኅዳሩ ላይ የምንሳተፍ ኃይሎች (መንግሥት፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ሲቪል ማኅበራት፣ የመገናኛ ብዙኋን፣ . . . እና መላው የሃገራችን ዜጎች) ሕጋዊ እና ሰላማዊ የሆነ ትግልን በመከተል እና ከዛ ውጪ ያለ አማራጭ የትግል መስመር ውስጥ ባለመሳተፍ እና ባለመደገፍ እንደሆነ እናምናለን። በተለይ በአሁኑ ሰዓት የሃገራችንን መሠረታዊ ችግሮችን ሥርዓት ለማስያዝ እንደሃገር ብዙ ተስፋ የሰነቅንበት ሃገራዊ ምክክር ሊጀምር በመሆኑ ትኩረታችን እሱ ላይ መሆን አለበት ብለን በጽኑ እናምናለን።
የሃገራዊ ምክክሩን ውጥኖች ተግባራዊነት በማረጋገጥ ነፃ፣ ፍትሃዊና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ መንግሥታዊ ሥልጣን የሚያዝበት ብቸኛው መንገድ እንዲሆን፣ እና ከዛ ውጪ ያሉት አማራጮች በኢትዮጵያ ምድር የማይሞከሩ ብቻ ሳይሆኑ የማይታሰቡም ጭምር እንዲሆኑ ማድረግ ያስፈልጋል ብለን እናምናለን።
በሃገር ውስጥም ሆነ ከሃገር ውጪ የሚገኙ አባላት እና ደጋፊዎች ከመርኀችን እና በግልጽ ካስቀመጥነው የሰላማዊ ትግል አቅጣጫችን በተለየ መንገድ መጓዝ የፓርቲውን ሕገ ደንብ በግልፅ መጣስ ከመሆኑም በላይ ከዘመን ዘመን ሲንከባለሉ የመጡ የሃገራችንን የፖለቲካ ችግሮቻችንም ሆነ ህዝባችንን አንገት ያስደፉ እና ለከፋ ድህነት እና ጉስቁልና የዳረጉ ስብራቶቻችንን በማባባስ ሂደት ላይ ከመሳተፍ ተለይቶ አይታይም።
ኢዜማውያን ይህን በውል በመገንዘብ ከሰላማዊ ትግል እና ከዜግነት ፖለቲካ እንቅስቃሴዎች ውጭ ያለን የፖለቲካ እንቅስቃሴ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ መደገፍ፣ የሀሳብም ሆነ የተግባር ተሳትፎም ሆነ ትብብር ማድረግ ከኢዜማዊነት መርኅ ማፈንገጥ መሆኑን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡
የፓርቲያችን ሊቀመንበር ጉዳይም ከዚህ ከላይ ከተገለፀው መርኅ አንጻር የሚታይ ይሆናል ሲል ፓርቲያችን ይገልፃል።
መስከረም 21/2016 ዓ.ም አዲስ አበባ ፣ ኢትዮጵያ
- ፖሊስ “ቴዎድሮስ በሚስቱ ሚዲያ ለምን ቤቱ ቅጭ ብሎ መግለጫ አይሰጥም ነበር?ዘፈኑ ገና ከመለቀቁ በፊት ጀምሮ በተከታታይ አየሩን የያዙት መረጃዎች ሁሉ በኦፊሳል ከቴድሮስ ካሳሁን፣ ከባለቤቱ ወይም በህግ የሚታወቁ ወኪሎቹና ተቋማትን ምንጭ ያደረጉ አልነበሩም።… Read more: ፖሊስ “ቴዎድሮስ በሚስቱ ሚዲያ ለምን ቤቱ ቅጭ ብሎ መግለጫ አይሰጥም ነበር?
- ቅዳሜ ምሽት በዋሽንግተን ዲሲ ሂልቶን፤ ሶስት ቀን የተደበቀው “ትኩላ” ዝርዝር ሪፖርትአዲስ ሪፖርተር ዜና – “ቅዳሜ ምሽት፤ በዋሽንግተን ዲሲ የሚገኘው ታዋቂው ሂልተን ሆቴል በደመቀ ድባብ ውስጥ ነበር። በመቶዎች የሚቆጠሩ ጋዜጠኞች፣ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት… Read more: ቅዳሜ ምሽት በዋሽንግተን ዲሲ ሂልቶን፤ ሶስት ቀን የተደበቀው “ትኩላ” ዝርዝር ሪፖርት
- “ኢሳያስ ከአሜሪካ ወዳጅነትን ይፈራሉ፤ ግንቡ ይፈርስባቸዋል” ቲቦር ናጊለሶስት አስርት ዓመታት በማዕቀብ ተቆልፎባት የኖረችው ኤርትራ በኢትዮጵያ ለውጥ መምጣቱን ተከትሎ ሰንሰለቱ ተበጥሶላት ነበር። ጦርነትም፣ ሰላምም ባልነበረበት ሁኔታ ተዘግቶባት የነበረችው ኤርትራ ከኢትዮጵያ… Read more: “ኢሳያስ ከአሜሪካ ወዳጅነትን ይፈራሉ፤ ግንቡ ይፈርስባቸዋል” ቲቦር ናጊ
- አውሮፓ ህብረት የጋራ መከላከያ ለማቋቋም የስምምነት ረቂቅ ሊያዘጋጅ ነውቪኦኢ ዜና -በአውሮፓ ህብረት እና በሰሜን አትላንቲክ ቃል ኪዳን ድርጅት (NATO) መካከል ያለው ግንኙነት ጥርጣሬ ውስጥ በወደቀበት በዚህ ወቅት፣ የአውሮፓ ህብረት አባል… Read more: አውሮፓ ህብረት የጋራ መከላከያ ለማቋቋም የስምምነት ረቂቅ ሊያዘጋጅ ነው
- የኢልሀን ኦማር የ30 ሚሊዮን ዶላር የሀብት መዝገብ እየተመረመረ ነው “የሂሳብ ስህተት ነው” ብላለችቪኦኢ ዜና -በአሜሪካ ምክር ቤት አባል ኢልሀን ኦማር የሀብት መግለጫ ላይ ታይቶ የነበረውና ከፍተኛ ውዝግብ አስነስተው የነበረው የ30 ሚሊዮን ዶላር ሃብት “የሂሳብ… Read more: የኢልሀን ኦማር የ30 ሚሊዮን ዶላር የሀብት መዝገብ እየተመረመረ ነው “የሂሳብ ስህተት ነው” ብላለች






