የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ለሰሊጥ አዝመራ የተመቸ አካባቢ ነው፡፡ በቀጣናው ነጩ ወርቅ እየተባለ የሚጠራው የሰሊጥ ምርት ለቀየው አርሶ አደሮች አንደኛ ደረጃ የሚባል የገቢ ምንጭ ነው፡፡ ምርቱ በተለይም ለውጭ ገበያም የሚቀርብ በመኾኑ የሚመለከታቸው አካላት በቅንጅት እስከ አዝመራ መሠብሠብ ድረስ የሚሠሩት ሥራ ነው፡፡
ነጭ ወርቅ እየተባለ የሚጠራውን ሰሊጥ ከሚያመርቱ ወረዳዎች መካከል ታች አርማጭሆ፣ ማዕከላዊ አርማጭሆ፣ ጠገዴ፣ አለፋ፣ ጣቁሳ፣ ጭልጋ፣ ነባሩ ጭልጋ፣ ምሥራቅ በለሳ፣ ምዕራብ በለሳ እና ኪንፋዝ በገላ ወረዳዎች ተጠቃሾች ናቸው፡፡
አርሶ አደር ይበልጣል አስተራይ በታች አርማጭሆ የሚኖሩ አርሶ አደር ናቸው፡፡ አርሶ አደሩ ዘንድሮ ለነጩ ወርቅ ትኩረት ሰጥተው ማሳቸውን መሸፈናቸውን ነግረውናል፡፡
አርሶ አደሩ እንደሚሉት በዚህ ዓመት ወደ አምስት ሄክታር የሚጠጋ የሰሊጥ አዝመራ እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡
በዚህ ዓመት በተቻለ መጠን ከግብርና ባለሙያዎች ጋር በተለያዩ የመገናኛ ዘዴዎች ተጠቅመው በምክረ ሃሳብ ማሳቸውን በሰሊጥ መሸፈናቸውን ገልጸዋል፡፡
አሁን ላይ አዝመራው ሲታይ የተሻለ ምርት እንደሚያገኙ ሰብሉ ካለበት ቁመና ተነስተው ያላቸውን ተስፋ ነው የተናገሩት፡፡
አርሶ አደሩ ሰሊጥ እንደደረሰ ጊዜ የማይሰጥ እና በቶሎ መሠብሠብ ያለበት አዝመራ በመኾኑ አጋዥ ሰው ያስፈልገዋል ነው ያሉት፡፡
አሁን ላይ ሰብሉ ሳይበላሽ በፍጥነት ለመሠብሠብ ጥረት እያደረጉ ቢኾንም አጋዥ ኀይል የሚያስፈልገው በመኾኑ የጉልበት ሠራተኛ ቢፈልጉም የሰው ኀይል ማግኘት እንዳልቻሉ ነው የተናገሩት፡፡ በማዕከላዊ ጎንደር ዞን አሁን ላይ የደረሰውን የሰሊጥ ሰብል ለመሠብሠብ የጉልበት ሠራተኛ እጥረት እንዳለም ነው የተገለጸው።
በማዕከላዊ ጎንደር ዞን የሰብል ልማት ቡድን መሪ ዮሃንስ ተስፋየ አሁን ላይ የሚሠበሠበው የሰሊጥ ሰብል በመኽር ከተዘራው 75 ሺህ 277 ሄክታር መሬት ላይ የተዘራ መኾኑን ተናግረዋል።
በዞኑ ነጩን ወርቅ ለመሠብሠብ ችግሮች ማጋጠማቸውን ነው የነገሩን፡፡ አንደኛው አሁን ላይ ዝናብ የመዝነብ ሁኔታ ስላለ እና ይህም የደረሰውን የሰሊጥ ምርት ስለሚያረግፈው በፍጥነት መሠብሠብ እንዳለበት ነው ያስረዱት፡፡ አቶ ዮሃንስ የጉልበት ሠራተኛ ከቦታ ቦታ አለመንቀሳቀስ ሰሊጡን በጊዜው ለመሠብሠብ እንቅፋት መኾኑን አስገንዝበዋል፡፡
የሰብል ቁመናው በጥሩ ደረጃ ላይ የሚገኝ በመኾኑ እና ያለምንም ብክነት ሰብሉን ለመሠብሠብ እስከ 30 ሺህ የጉልበት ሠራተኛ ለዞኑ ብቻ እንደሚያስፈልግ ነው የተናገሩት፡፡ ምርቱን በሚገባ ሠብሥቦ ለሀገር ጥቅም ለማዋል ሁሉም የጉልበት ሠራተኞች እንዲንቀሳቀሱ ትብብር እንዲያደርግ አሳስበዋል፡፡ በዚህ ሥራ ላይ የጉልበት ሠራተኞች እንዲሳተፉም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
የሰሊጥ ልማቱ ላይ 24 ሺህ 526 በላይ አርሶአደሮች እየተሳተፉ እንደሚገኙ የገለጹት የሰብል ልማት ቡድን መሪው ከዚህ ውስጥ 1 ሺህ 453 የሚኾኑት ሴቶች መኾናቸውን ተናግረዋል፡፡
ምርቱ በዓለም ገበያ አዋጭ በመኾኑ የምርት ብክነት እንዳያጋጥምም ትኩረት ተደርጎ እየተሠራ ነውም ብለዋል።
በዞኑ ለምቶ ከሚሠበሠበው የሰሊጥ ሰብልም 602 ሺህ 216 ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ከዞኑ ግብርና መምሪያ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል። (አሚኮ)

