የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የአሜሪካ የጦር አውሮፕላኖች ኢራን ውስጥ የሚገኙ ሦስት የኒውክሌር ተቋማትን በቦምብ መደብደባቸውን ማሳወቃቸው ይታወሳል።
አሜሪካ “የእኩለ ሌሊት መዶሻ” የሚል ስያሜ በሰጠችው ኦፕሬሽን ጂቢዩ 57 ወይም ማሲቭ ኦርዲናንስ ፔኔትሬተር (ኤምኦፒ) ቦምብ ተጠቅማለች፡፡
ይህ ‘ምሽግ ደርማሽ’ ቦምብ 13 ሺህ 600 ኪሎ ግራም የሚመዝን ሲሆን ከመፈንዳቱ አስቀድሞ እስከ 60 ሜትር ድረስ ወደ መሬት ሰርጎ የመግባት አቅም ያለው ነው፡፡
ቦምቡ ‘ B-2’ በተባለው ስውር ቦምብ ጣይ አውሮፕላን አማካኝነት ከዒላማው ከ12 ሺህ እስከ 15 ሺህ ሜትር ከፍታ ላይ የተጣለ ሲሆን፣ ያለው ክብደት እና የመሬት ስበት በሚያርፈበት ቦታ ላይ ውድመት እንዲያስከትል ያደርጉታል፡፡
የተቀመጠለትን ዒላማ እንደማይስት የሚነገርለት ‘ምሽግ ደርማሹ’ ቦምብ በውስጡ በተገጠመለት ጂፒኤስ በመጠቀም ነው ጥቃቱን የሚያደርሰው፡፡
በዚህም ከተጣለ በኋላ ምንም ዓይነት የዒላማ ለውጥ ወይም ቁጥጥር ማድረግ አይቻልም፡፡
የአንዱ ዋጋ ከ3.5 እስከ 4 ሚሊዩን ዶላር እንደሚደርስም ተመላክቷል፡፡
ይህንን ግዙፍ ቦምብ መሸከም የሚችለው ‘B-2’ ስውር ቦምብ ጣይ አውሮፕላን በያዘው ቅርፅ ምክንያት በተለይም በፀረ-አውሮፕላን አነፍናፊ መሳሪያ ወፍ ወይም በራሪ መስሎ መታየት ያስችለዋል፤ በዚህም በዒላማ ማክሸፊያ እንዳይመታ እንደሚያደርገው ይነገራል፡፡
በተጨማሪም ትክክለኛ ያልሆነ የራዳር መረጃ የሚያቀብል የኤሌክትሮኒክ ቴክኒክ ያለው ነው፡፡
ሌላው አሜሪካ የተጠቀመችው ከ1 ሺህ 600 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ መወንጨፍ የሚችሉት የ’ቶማሃውክ ክሩዝ’ ሚሳኤሎች ናቸው፡፡
ከሰርጓጅ መርከብ ላይ የተነሱት ሚሳኤሎቹ ከምድር በታች ያልሆነ ማለትም በምድር ላይ ያለ ዒላማን ለማጥቃት የሚውሉ ናቸው፡፡
በአሜሪካ የ“ሌሊት መዶሻ ኦፕሬሽን” 30 የሚሆኑ የ’ቶማሃውክ ክሩዝ’ ሚሳኤሎች ከ640 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ መወንጨፋቸው ተገልጿል፡፡
በራዳር ዕይታ ውስጥ እንዳይገባ በዝቅተኛ ከፍታ ላይ መንሳፈፍ የሚችለው ሚሳኤሉ፣ ከተወነጨፈ በኋላ የዒላማ ብሎም የአቅጣጫ ቅየራ እንዲያደርግ ማዘዝ ይቻላል፡፡ እያንዳንዱ ‘ቶማሃውክ ክሩዝ’ ከ1.5 እስከ 2 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ዋጋ ያለው ነው፡፡ አሜሪካ በኢራን በፎርዶ፣ ናታንዝ እና ኢስፋሃን የኒውኩሌር ማበልፀጊያዎች ላይ ነው ጥቃቱን የፈጸመችው፡፡ ኢዜአ

