በአዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ስደተኛ ላልሆኑ እና ወደ ዩናይትድ ስቴት መጓዝ ለሚፈልጉ ኢትዮጵያውያን የሚሰጠው ጊዜያዊ ቪዛ የሶስት ወራት ብቻ እንደሚሆን አስታወቀ። በዚህ የአጭር ጊዜ ቪዛ ኢትዮጵያውያን ወደ አሜሪካ መግባት የሚችሉት አንድ ጊዜ ብቻ እንደሚሆን ኤምባሲው ባወጣው መግለጫ ይፋ አድርጓል።
እርምጃው ከሐምሌ 1 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ መሆኑን የገለጸው የአሜሪካ ኤምባሲ ውሳኔው ከዚያ በፊት የተሰጡ ቪዛዎች ላይ ተጽዕኖ እንደማያሳድር አረጋግጧል። እስካሁን የነበረው አሠራር የተቀየረው የአሜሪካ ውጪ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ስደተኛ ያልሆኑ ሰዎች የቪዛ አሰጣጥ ፖሊሲ ላይ ባደረገው ለውጥ ምክንያት እንደሆነ የኤምባሲው መግለጫ ይጠቁማል።
ስደተኛ ላልሆኑ ሰዎች የሚሰጥ ቪዛ የሌሎች ሀገራት ዜጎች ለቱሪዝም፣ ለንግድ፣ ለሕክምና እና የተወሰኑ ቋሚ ያልሆኑ ሥራዎች በጊዜያዊነት ወደ አሜሪካ እንዲገቡ የሚፈቅድ ነው።
እስካሁን ድረስ ኢትዮጵያውያን የሚያገኙት ቪዛ ወደ አሜሪካ በተደጋጋሚ እንዲገቡ የሚፈቅድ (multiple-entry) እና እስከ አንድ አመት የሚቆይ ነበር። አዲሱ ገደብ በተለይ ተማሪዎች ፣ ነጋዴዎች፣ ባለሙያዎች እና ከቤተሰብ ጋር ለመገናኘት የሚጓዙ ሰዎች ላይ ተጽዕኖ ያሳድራል።
በጎርጎሮሳዊው 2024 ብቻ በአዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ 23,270 ቪዛ ስደተኛ ላልሆኑ ሰዎች እንደሰጠ ዩናይትድ ስቴትስውጪ ጉዳይ መሥሪያ ቤት መረጃ ያሳያል። በመሥሪያ ቤቱ መረጃ መሠረት በአፍሪካ የሚገኙ የአሜሪካ ኤምባሲዎች በዓመቱ በአጠቃላይ 343,075 ቪዛ ስደተኛ ላልሆኑ ሰዎች ሰጥተዋል።

