አንዳንድ ሚዲያዎች “ኢትዮጵያ ይህን ጉባኤ እንዴት እንዳዘጋጀቸው ባይታወቅም” በማለት እየተብሰለሰሉ ሽፋን ሰጥተውታል። ከጉባኤው ጀርባ አገርና ሕዝብ የሚጎዳ አጀንዳ ያለው ለማስመሰል እየዳዳቸው እንግዶቹ ከአለባበስ ጀምሮ መሳቂያ አድርገዋቸዋል። ይህ ታላቅ ስብሰባ እንዲዘጋጅ ኢትዮጵያ ተነሳሽነቱን ስትወስድ በአፍሪካ “የምግብ ሉዓላዊነት” አጀንዳ ለመትከልና አጀንዳውን በማሳካት ልክ እንደ አደዋ ዓይነት ታሪክ ለመጻፍ መነሳቷ የገባቸው “የአፍሪካን ስርዓተ ምግብ ከቅኝ ግዛት እሳቤዎች ነፃ ማውጣት ይገባል” በሚል አሳቡን ወርቅ ሲቀቡት ታዝበናል።
ሁለተኛውን የዓለም የምግብ ሥርዓት ጉባዔ ከእሁድ ሐምሌ 20 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። ያዘጋጁት ደግሞ ኢትዮጵያ እና ጣሊያን በጋራ ሲሆን፣ ከአራት ዓመታት በፊት በመንግሥታቱ ድርጅት ዋና ፀሐፊ ቢሮ በኩል ተዘጋጅቶ ዕውቅና የተሰጠው ታላቅ ጉባኤ ነው። ይህ ጉባኤ የዛሬ ሁለት ዓመት የመጀመሪያው የዓለም የምግብ ሥርዓት ጉባኤ (UNFSS+2) በሮም ጣሊያን በዓለም ምግብ እና እርሻ ድርጅት ዋና መሥሪያ ቤት መካሄዱ የሚታወስ ነው።
በወቅቱ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የ FAO አግሪኮላ ሜዳልያ መሸለማሸው የሚታወስ ነው። ሽልማቱን ያገኙት በጥር 28 ቀን 2024 ዓ.ም ነበር። ሽልማቱን የ FAO ዋና ዳይሬክተር QU Dongyu ነበር ያበረከቱላቸው። ሜዳልያው ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በኢትዮጵያ በገጠርና ኢኮኖሚ ልማት በተለይም በምግብ ዋስትና እና በስነ-ምግብ ዘርፍ ላበረከቱት አስተዋፅኦ እና በስንዴ እራስን መቻል ላሳዩት የሚጨበጥ ስራቸው እንደነበር በወቅቱ መገለጹ የሚታወስ ነው።
ዋና ዳይሬክተሩ ሽልማቱን ሲያበረክቱ እንዳሉት ሜዳሊያው የተሰጠው ለኢትዮጵያና አፍሪካ እንጂ ለተቅላይ ሚኒስትር አብይ ብቻ እንዳልሆነ ገልጸዋል። ይህን ሽልማት ሲሰጡ የተሰማቸው ደስታና ክብርም ትልቅ መሆኑ አስታውቀው ነበር። ይህን ሽልማት ተክትሎ “ተፈናቃይ አለ፤ ተረጂ አለ። ረሃብተኛ አለ” ወዘተ በማለት በሌላ ወገን ያሉ ለማናናቅ ሞክረው እንደነበር ይታወሳል።
“ድሃ ይሁን ሀብታም፤ ልጅ ይሁን አዋቂ በዚህ ዓለም ሁሉም ሰው ምግብ ማግኘት አለበት። ደኅንነቱ የተጠበቀ እና የተመጣጠነ ምግብ ሕይወት ብቻ ሳይሆን ጤና እና ተስፋም ነው” በሚል ጥልቅ እሳቤ እየተካሄደ ያለው ጉባኤ አስመልክቶ ንግግር ያደረጉት አብይ አህመድ፣ የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ ከምግብ ሥርዓት ጋር እንዲጣጣም ጥሪ ሲያቀርቡ ተሰምተዋል።
በዋረንጓዴ ሌጋሲ መርህ ከቀናት በሁዋላ ስልሳ ሚሊዮን ችግኝ በአንድ ቀን ለመትከል ዝግጅቷን ያጠናቀቀችው ኢትዮጵያ ከጣሊያን ጋር በትብብር ባዘጋጀችው በ2ኛው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የምግብ ስርዓት ጉባኤ መክፈቻው ላይ ንግግር ያደረጉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ፣ ለልማት የሚደረጉ ድጋፎች በመቀዛቀዛቸው ምክንያት አፍሪካ ጫና ውስጥ እንደምትገኝ እና የባለብዙ ወገን ግንኙነቶች ፈተና እንደገጠማቸውም ገልፀዋል፡፡ አክለውም አፍሪካ በግብርና፣ የገጠር ልማት፣ መሠረተ ልማት እና ቢዝነስ ላይ ኢንቨስት እንድታደርግ ተገማች ፋይናንስ ያስፈልጋታል ብለዋል፡፡
“ከእኛ አውድ ጋር የሚስማሙ ከአየር ንብረት ጋር የተዛመኑ መሳሪያዎች፣ ባዮቴክኖሎጂ እና የዲጂታል ግብርና ያስፈልጉናል። ቴክኖሎጂዎች ተመጣጣኝ እና የጋራ ሊሆኑ እንጂ ሊደበቁ አይገባም” ሲሉ አጽዕኖት ሰጥተዋል።
በኢትዮጵያ እና በጣሊያን ትብብር የሚካሄደው የመሪዎች ጉባኤ ቀጣይነት ያለው፣ አካታች እና የማይበገር የምግብ ስርዓት ግንባታ ላይ አተኩሮ ከሐምሌ 20 እስከ 22 ድረስ ይካሄዳል፡፡
በዚሁ ጉባኤ ላይ “የአፍሪካን ስርዓተ ምግብ ከቅኝ ግዛት እሳቤዎች ነፃ ማውጣት ይገባል” ሲሉ የሳህል ድርቅ ቁጥጥር የሀገራት ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ዋና ጸሃፊ ዶ/ር ሲልቫን ናፊባ ኦውድራጎ፤ በአሕጉሪቱ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በግብርናው ዘርፍ ያሉ ሀገር በቀል ዕውቀቶችን በአግባቡ መመርመር አንደሚገባ፤ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ካለው የተመድ የምግብ ሥርዓት ጉባኤ ጎን ለጎን ለስፑትኒክ አፍሪካ ገልጸዋል።
“ያለ አገር በቀል ዕውቀት የምግብ ስርዓታችንን ማሻሻል አንችልም። ምክንያቱም ከዘመናዊ ግብርና በፊት ለዘመናት ይህ ዕውቀት መሬት ላይ ነበር። ይህን አገር በቀል ዕውቀት በትክክል ልናጠናው እና እንዴት ልናስተዋውቀው እንዲሁም በሳይንስ ደረጃ ልናስቀምጠው እንደምንችል መፍትሔ ልናበጅ ይገባል” ብለዋል።
በተባበሩት መንግሥታት የምግብ ሥርዓቶች ጉባኤ ላይ የተገኙ የተለያዩ ሀገራት መሪዎች የአረንጓዴ ዐሻራችውን አኖሩ
ሁለተኛው የተባበሩት መንግስታት የምግብ ሥርዓት ጉባኤ የመክፈቻ መርሃ ግብር በአዲስ አበባ የተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን አዳራሽ መካሔድ ጀምሯል።
የግብርና ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) እና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ምክትል ዋና ጸሀፊ አሚና መሀመድ ለመገናኛ ብዙሀን ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።
የግብርና ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ መድረኩ በዘመናችን ካሉት እጅግ አንገብጋቢ ፈተናዎች አንዱ የሆነውን የአየር ንብረት ለውጥ ለመቋቋም አለም አቀፍ ቁርጠኝነት ማሳያ ነው።
ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ዓለማችን ከዚህ በፊት ታይቶ የማይታወቅ ከአየር ንብረት ለውጥ እንዲሁም ጂኦፖለቲካዊ ግጭቶች እና የኢኮኖሚ ተለዋዋጭነት እየገጠማት መሆኑን ገልጸዋል
እነዚህ ተግዳሮቶች የምግብ ስርዓት የሚፈለገውን ያህል የመቋቋም አቅም እንደሌለው ማረጋገጣቸውን ገልጸው፤ የጋራ ጥረትን በእጥፍ ለማሳደግ ይህ ጉባኤ ወሳኝ ነው ብለዋል።
በመስክ ጉብኝቱ ላይ የተሳተፉ ልዑካን በምግብ ስርዓት ለውጥ ግንባር ቀደም ካሉት ሰዎች በመሬት ላይ ያለውን ፈጠራ እና ተግዳሮቶች በዓይናቸው ማየት መቻላቸውን አንስተዋል።
ኢትዮጵያን ጨምሮ ከፍተኛ እመርታ እያሳዩ ያሉ ሀገራት የ2030 የዘላቂ ልማት ግቦች ላይ ለመድረስ ጥረታችንን ማፋጠን አለብን ብለዋል።
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ምክትል ዋና ጸሀፊ አሚና መሀመድ እንደገለጹት፤በርካታ ሀገራት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተለያዩ እርምጃዎች እየወሰዱ ናቸው።
እንዲሁም መንግስታት በዚህ ላይ ፖሊሲና ስትራቴጂ ቀርጸው እየተገበሩ መሆናቸው በሪፖርት መመላከቱን ጠቁመዋል።
ትናንት ባደረጉት ጉብኝት ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ እያከናወነቻቸው ያሉ ስራዎች አስደናቂ መሆናቸውን ለመመልከት መቻላቸውን አንስተዋል። የአመራሩን ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑን ጠቅሰዋል። ባለብዙ ወገን ግንኙነትን ማጠናከር ወሳኝ መሆኑን ገልጸው፥ይህም አለም አቀፋዊ ቀውሶች ሲያጋጥሙ መውጫ መንገድ መሆኑን አብራርተዋል።





