ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ጥቁሮች እንደምንችል እና እንደምናሳካ ያሳየንበት ታላቅ ስራ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)ገለጹ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የኢትዮጵያውያን ሕብረ ብሔራዊነት መገለጫ የሆነውን ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን ዛሬ ጳጉሜን 4 ቀን 2017 በይፋ መርቀዋል፡፡
በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ታገሰ ጫፎ፣ የፌደሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አገኘሁ ተሻገር፣ ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው፣ የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝደንት አቶ ቴዎድሮስ ምህረት፣ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ፣ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማሪያም ደሳለኝ፣ የሀይማኖት አባቶች ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡
በተጨማሪም የጂቡቲው ፕሬዚዳንት ኦማር ጌሌ፣ የደቡብ ሱዳን ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር ማያርዴት፣ የሶማሊያው ፕሬዚዳንት ሀሰን ሼክ መሐሙድ፣ የኬንያው ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ፣ የባርቤዶስ ጠቅላይ ሚኒስትር ሚያ ሞትሊ፣ የስዋቲኒ ጠቅላይ ሚኒስትር ሚሶ ድላሚኒ፣ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ማሕሙድ ዓሊ ዩሱፍ፣ የተመድ ምክትል ዋና ጸሐፊ እና በተመድ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ክላቨር ጋቴቴ ተገኝተዋል፡፡
በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ ንግግር ያደረጉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያውያን እንኳን ለዚህ ቀን አደረሳችሁ ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያዊያን በህዳሴ ግድብ ታሪክ ሰርተን ታሪክ ላይ ቆመን ለማውራት በቅተናል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ህዳሴ የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የመላው ጥቁር ህዝቦች ታሪክ ሆኖ የሚኖር ነው ብለዋል፡፡
ባለፉት ዓመታት አባይ እግር እንጂ አፍ አልነበረውም፣ ለዚህም ኢትዮጵያዊያን ሲያወሩለት ነበር ዛሬ ግን አባይ ራሱ ማውራት ጀምሯል ብለዋል፡፡
ሁሉም ኢትዮጵያዊያን በጉባ ተገኝተው ይህን ታሪክ፣ ገድል፣ ማየት አለባቸው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህን የትውልድን ገድል ሁሉም መመልከት አለበት ብለዋል፡፡
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ጥቁሮች እንደምንችል እና እንደምናሳካ ያሳየንበት ታላቅ ስራ ነው ብለዋል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የትናንት ቁጭት ማሰሪያ የመጪው ንጋት ማብሰሪያ መሆኑን አንስተው ባለፉት አምስት ዓመታት 74 ትሪሊዮን ሊትር ውሃ መያዝ መቻሉን ጠቁመዋል፡፡
የኢትዮጵያን ጥልቅ ጨለማ፣ ከጥልቅ እንቅልፍ ያነቃ በመሆኑ የተያዘው ውሃ ንጋት መባሉን ጠቁመዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብልጽግና እና ልክ አይቀሬ መሆኑን ጠቁመው፤ ኢትዮጵያ ትበለጽጋለች፤ ኢትዮጵያ ተረጂነቷ አብቅቶ ረጂ ሀገር ትሆናለችም ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ የማንሰራራት ዘመን ከኛ ጋር የተገኙ ወዳጆቻችን ኢትዮጵያ ካላት ነገር ሁሉ ታቋድሳችኃላች ብለዋል፡፡
ለታችኛው የተፋሰስ ሀገራት ኢትዮጵያ ህዳሴን የገነባችው ለመበልጸግ እና አካባቢውን በብርሃን ለመሙላት እንዲሁም የጥቁር ህዝብን ታሪክ ለመቀየር እንጂ በፍጹም ወንድሞቿን ለመጉዳት አይደለም ብለዋል፡፡
ለወደፊት በምንሰራቸው ታላላቅ ስራዎች በትብብር በጋራ እንድንቆም ከአደራ ጭምር ላሳስባችሁ እወዳለው ብለዋል፡፡ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ገደሉን ተሻግረናል፣ ገድል በህዳሴ አትመናል ብለዋል፡፡
በሌላ ዜና ተመሳሳይ ዜና የኢፌዴሪ አየር ኃይል አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

ለዘመናት የለፋንበት የኢትዮጵያ ከፍታ ማብሰሪያ የሁሉም ኢትዮጵያዊ አሻራ ያረፈበት ግድብ ለምርቃት መብቃቱን ጠቅሰው፤ በቦታው ተገኝተው ይህን በማየታቸው እንደ አንድ የሀገር ጦር መሪ ትልቅ ኩራት እንደተሰማቸው ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ አየር ኃይል የግድቡ መሠረተ ድንጋይ ሲጣል ጀምሮ ለምርቃት እስከበቃበት ጊዜ ድረስ የቀጠናውን የአየር ክልል በአስተማማኝነት በመጠበቅ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
ካለፉት ዓመታት በተለየ ሁኔታ ተቋሙ የምድር አየር መከላከል አቅም ማሳደጉን ገልጸው፤ በሰማይ የጠላትን ዒላማ በአስተማማኝ ሁኔታ ገና ከመነሻቸው ማውደም የሚችሉ ተዋጊ የጦር ጄቶችን መታጠቁን ገልጸዋል፡፡
ግዳጅን ባጠረ ጊዜ በላቀ ብቃት የመፈፀም እምቅ አቅምና ቴክኖሎጂውን መጠቀም የሚችል የሠው ኃይል በማደራጀት በማንኛውም ሰዓት የአየር ክልሉን የማያስደፍር የሀገር ኩራት የሆነ አየር ኃይል መገንባቱንም ተናግረዋል፡፡
ዘገባው የኢዜአ ነው

