ፎቶው ላይ የሚታዩት ግለሰቦች በንጽጽር ከተለያየ የህይወት ጥጎች የመጡ ቢሆንም ፥ በዚህ ፎቶ ላይ የሁሉም ፊት ሀዘንና ቁዘማን አዝሎ ይታያል። ፎቶው የተነሳው በስደት ላይ ሲሆን ፤ ግራይዚያኒ ላይ የደረሰው የመግደል ሙከራን አስከትሎ ለሶስት ቀናት የተደረገው የየካቲት 12 ጭፍጨፋ ለመዘከር በተሰበሰቡበት ወቅት ነው።
በግራ ጥግ ቆመዉ የሚታዩት የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት የነበሩት ቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ ናቸው። በወቅቱ የፋሽስት ጦር በአድዋ ድል አቂሞ ለ40 ዓመታት ያህል የያዘውን ቂም ለመበቀል ያሰናዳውን ዘመናዊ የጦር መሳሪያዎችን እንዲሁም በዓለም አቀፍ ዙሪያ የተከለከለውን ፣ በታሪክም ለመጀመሪያ ጊዜ ኢትዮጵያ ላይ ለጭፍጭፋ የዋለውን የMustard Gas መቋቋም ኢትዮጵያኖችን እንዳቃታቸው የተረዱት የዘውድ አማካሪዎችና በወቅቱ ወጣትና የብሩህ አእምሮ ባለቤት የሆኑ የፖለቲካ ስብዕናዎች ፣ በብዙ መከራ ንጉሱን ለምነው ውጭ ሀገር ሄደው ኢትዮጵያ ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍ ለዓለም መንግስታት እንዲያስረዱ ፤ ጄኔቭ ላይ ከተባበሩት መንግሥታት ፊት ቀርበው ይህን በማስረዳት እርዳታ ይዘው እንዲመጡ በአቡኑ አስገዝተው በኢትዮጵያ ታሪክ በጦርነት ሰዓት ሀገርን ለቀው ወደ ውጭ የተሰደዱ የመጀመሪያ ንጉሠ ነገሥት ለመሆን በቅተዋል። (ምንም እንኳን ማይጨው ላይ ያደረጉት ተጋድሎ ባይረሳም) …
እሳቸው ያደጉበት ባላባታዊ ወግና ባህል ፥ እንዲሁም ሁሉንም ነገር በድፍረት ፊት ለፊት መጋፈጥ የለመደ ደፋርና ጦረኛ ህዝብ ፣ አድዋ ላይ ቀድሞ ላሸነፈው ፣ በብዙ በኩል ለናቀው ለጦሊያን ጦር ፣ ፊት ለፊት እየመራ የሚዋጋው ንጉሥ እንጂ ለህዝቡ ደህንነትም ቢሆን የንጉሱን ዲፕሎማሲያዊ ትግል የሚረዳበት ንቃተ ህሊና ወይም እርጋታ አልነበረውም። በዚህም ምክንያት በአንዳንድ አርበኛ መኳንንቶች ይህ ዲፕሎማሲያዊ ትግላቸው እንደ ፈሪነት ወይም ፈርጣጭነት ተቆጥሮባቸዋል። በተጨማሪም ‘ለኢትዮጵያ እርዳታ ያስገኛል’ ተብሎ የታቀደለት የጄኔቭ ስብሰባ ንግግራቸው : በፈረንጅ ፊት መሳለቂያ ያደረጋቸው መሆኑ ፤ እንግሊዝ በሚኖሩበት ሰዓት የገንዘብ እጥረት እያጋጠማቸው የቤተሰባቸውን የስደት ኑሮ ለማስቀጠል ፊት ማየታቸውን – የግል ንብረቶቻቸው የሆኑ እቃዎቻቸውን ለመሸጥ መገደዳቸውና ሌሎቹ ምክንያቶች ተዳምረው ንጉሱን በስደት ጊዜያቸው ሀዘንተኛ እንደነበሩ በቅርብ ለማወቅ የቻሉ የባዝ ኢንግላንድ ነዋሪዎች በተለያዩ መጽሐፍትና ዘጋቢ ፊልሞች ላይ የግል ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል።
ከንጉሡ አጠገብ የሚታዩት ልዑል ራስ ካሣ ኢትዮጱያ ውስጥ ከነበሩ ትልቅ ባላባቶች ውስጥ ቀዳሚ የነበሩና በመንግስት ፖለቲካ ላይ ትልቅ ተሰሚነት የነበራቸው ናቸው። በጦርነቱ ላይ የራሳቸውን ጦር አዝምተው ቢሆንም ፤ ከማይጨው ሽንፈት በኋላ ከንጉሱ ጋር ወደ ውጭ ተሰደዋል። ኢትዮጵያ ውስጥ ከቀሩት በአርበኝነት ሀገራቸውን ሲያገለግሉ የነበሩት ልጆቻቸው ውስጥ ደጃዝማች ወንደሰንና ደጃዝማች አበራ ካሳ በራስ ኃይሉ ምክር ለጣሊያኖች እጃቸውን እንዲሰጡ ተመክረው ወዲያው በጥይት ተደብድበው ሞተዋል። ፊታቸውም የማይፈታው ሁለት ልጆቻቸውን በግፍ ስላጡ እንደነበር በሰዎች ዘንድ ይነገራል።
ከልዑል ራስ ካሳ አጠገብ የሚታዩት ደግሞ ሀኪም ወርቅነህ ወይም ሻርለስ ማርቲን ናቸው። አፄ ቴዎድሮስን ያሸነፈው የኢንግሊዝ ጦር መቅደላ መሬት ላይ ሲጫወቱ አይቷቸው ወደ ከልጅ አለማየሁ ጋር ወደ ውጭ ሀገር በጨቅላነታቸው ተጉዘዋል። ባገኙትም ዘመናዊ ትምህርት በኢትዮጵያ ታሪክ የመጀመሪያው ዘመናዊ የኢትዮጵያ ሀኪም ለመሆን በቅተዋል። ኢትዮጵያ ወደ ዘመናዊነት ዓለም እንድትቀላቀል ብዙ ትግል ያደረጉት እኝህ ግለሰብ ፣ ከንጉሱ ጋር ወደ ውጭ ተሰደው ህይወታቸውን ቢያተርፉም ፤ በአብርሃም ደቦጭና ሞገስ አስገዶም መሪ ተዋናይነት የተቀነባበረው ማርሻል ግሪዚያኒን የመግደል ሙከራ አዲስ አበባ ላይ ካስጨፈጨፋቸው የስላሳ ሺህ ሰዎች መካከል የሳቸውም ወንድ ልጆች የነበሩት ዩሴፍ እና ቢንያም ወርቅነህ ሊገደሉ ችለዋል።
በግራ በኩል ጥግ ላይ መንጽራቸውን አድርገው ሲተክዙ የሚታዩት “የኢትዮጵያ የስነጽሁፍ አባት” ተብለው የሚጠሩት ብላቴን ጌታ ህሩይ ወልደስላሴ ናቸው። ፎቶዉ ላይ ቆመው ከሚታዩት ግለሰቦች በተለየ ዝቅተኛ ከሚባለው የማህበረሰብ ክፍል የመጡ ሲሆን ፥ በቤተክህነት ትምህርት ላይ ላቅ ያለ እውቀት ስለነበራቸው አንዱ መምህራቸው “አንተ የቀለም ቀንድ ስለሆንክና በምግባርህም የተመሰገንህ ነህና፡ ኅሩይ የተባለውን ስሜን ሸልሜያሃለሁ፡ ከንግዲህ ኅሩይ እየተባልክ ተጠራ” ብለው <<ገብረመስቀል>> የተሰኘውን የትውልድ ስማቸውን እንዲተዉ አድረጋዋቸዋል። በመጨረሻም በደራሲነት ፣ በዲፕሎማሲው ዘርፋና በተለያዩ የመንግስት ስራዎች ላይ በመሳተፍ ለቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግስትና ለኢትዮጵያ ትልቅ አስተዋጽኦ ለማድረግ የበቁት ብላቴን ጌታ ህሩይ ፣ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ወደ ውጭ እንዳይጓዙ ከመረጡት የመንግስት ቧለሟሏች ውስጥ አንዱ ቢሆኑም ፤ የንጉሰ ነገስቱ ወደ ውጭ መሄድ እርግጥ በሆነበት ሰዓት ተቀላቅለዋቸው ተሰደዋል። በስደት ዘመናቸውም ለኢትዮጵያ በጣም ይጨነቁ እንደነበርና – ይህም ለሞታቸው አስተዋጽኦ እንዳደረገ ይነገራል። ሥርዓተ ቀብራቸው መስከረም 10 ቀን እዚያው እንግሊዝ አገር ሲፈጸም ንጉሠ ነገሥቱ የሚከተለውን ንግግር አደረጉ:-
«አሁን የአዳምን ልጆች ወግ ሲቀበል የምታዩት ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደሥላሴ በአገራችን ሥርዓት በመልካም አያያዝ ያደገ ከኢትዮጵያም ከፍ ካሉት ሊቃውንት የሚቆጠር ነው። ብልሃቱንና ትጋቱንም ለመልካም ሥራ የሚያገለግሉ መሣሪያዎች ስላደረጋቸው በመንግሥታችን ሥራ ለመመረጥና ወደ ታላቁ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት ለመድረስ በቃ። በየጊዜው የጻፋቸው ከፍትኛ ባህሪውን የሚገልጹ መጻሕፍት፤ ይልቁንም በቤተ ክህነትና በታሪክ እውቀት በዓለም ሊቃውንት ዘንድ የታወቀና የተከበረ አደረጉት። ለምታውቁት ሰው ከታሪኩ ከዚህ የበለጠ ልነግራችሁ የሚያስፈለግ አልመሰለኝም።
በአጭሩ ከጠባዩ ትልቅነት የሚሰማኝን ለመናገር ሳስብ ጊዜውን ሁሉ ቁም ነገር በመሥራት ማሳለፉ፤ ከራሱ ይልቅ የተቸገሩትን ለመርዳት መጣሩ፤ እውነትን፣ ፍርድንም ማክበሩና በአገር ፍቅር መቃጠሉ ትዝ ይሉኛል።
አገልጋዬና ወዳጄ ኅሩይ! በተቻለህ ስለአገርህ ሥራህን በሚገባ ፈጽመህ በምትሰናበትበት ጊዜ ታላቅ ነህ ሳልልህ ብቀር ሥራዎችህ ቀድመውኝ ይናገራሉ። በክፉ አድራጊዎች የሚገፋ የዓለምን ፀጥታ የሚያናውጥ ነፋስ ምንም ቢያንገላታህና በታላቅ ፈተና ላይ ቢጥልህም ሊያሸንፍ አልቻለም። ታላቅና ቸር በሆነው ጌታ በተመደበው ሕግ ግን መታዘዝ ግድ ሆነብህ። ይህም ለያንዳንዳችን የሚደርሰን ዕድል ነው። አንተም እስከ መጨረሻ ከታገልክ በኋላ ዛሬ ደከመህ፣ አንቀላፋህም። በሥጋ ብትለየንም ስምህና ሥራህ በመካከላችን ይኖራሉ።
ኅሩይ! እግዚአብሔር ሲያስበን አጥንቶችህና መንፈስህ የሚሰፍሩበትን ቦታ እስኪያዩና ከአባቶችህ እስኪቀላቀሉ ድረስ በእንግድነት በመጣህበት በዚህ ሥፍራ በሰላም ዕረፍ።»
©Zerraf Metsiha Medebir Ethiopian History and Tourism/የኢትዮጵያ ታሪክና ቱሪዝም

